Tuesday, September 25, 2018

ለፍርድ አንቸኩል!

ማክስ ሉካዶ የታወቀ አሜሪካዊ ጸሐፊ፣ ሰባኪ እና ተናጋሪ ነው፡፡ ከጻፋቸው በርካታ መጻሕፍት  መካከል “The Woodcutter’s Wisdom & Other Favorite Stories” በሚል ርዕስ እ.ኤ.አ. በ2005 ዓ.ም. የታተመው መጽሐፍ አንዱ ነው፡፡
በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የሚገኘው እና የመጽሐፉ መጠሪያ የሆነው “The Woodcutter’s Wisdom” የሚለው አጭር ታሪክ ለአሁኑ የአገራችን ተለዋዋጭ የፖለቲካ ሁኔታ እና ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን ምላሽ ጥሩ ምክር የሚሰጥ ይመስለኛል (ይህ አጭር ታሪክ “ዛፍ ቆራጩ” በሚል ርዕስ በአማርኛ ተተርጉሞ ታትሟል፣ በሸገር ኤፍ ኤም የ”ሸገር ሸልፍ” ፕሮግራም ላይም አንዱዓለም ተስፋዬ አቅርቦት ነበር)፡፡
ታሪኩ በአጭሩ እንዲህ ነው፡፡
በአንዲት አነስተኛ መንደር የሚኖር አንድ ሽማግሌ ዛፍ ቆራጭ ነበር፡፡ ይህ ሽማግሌ ደሃ ቢሆንም በጣም የሚያምር ፈረስ ስለነበረው በርካታ ሰዎች (የአገሩን ንጉሥ ጨምሮ) ፈረሱን እንዲሸጥላቸው ከፍ ያለ ገንዘብ ይዘው ደጅ ይጠኑት ነበር፡፡ የሽማግሌው ምላሽ ግን “ይህ ፈረስ ለእኔ ፈረስ አይደለም፣ ሰው ነው፣ ጓደኛዬ ነው፡፡ ጓደኛ እንዴት ይሸጣል?” የሚል ነበር፡፡
እንድ ቀን ጠዋት ላይ ሽማግሌው ጋጣውን ሲያይ ባዶ ነው፣ ፈረሱ የለም! ይህንን የሰሙ የመንደሯ ሰዎች ተሰብስበው ወደሽማግሌው ቤት መጡና “አንተ ሞኝ ሽማግሌ! ፈረስህ ሊሠረቅ እንደሚችል ነግረንህ ነበር፡፡ ያኔ ሸጠኸው ቢሆን ኖሮ ይሄኔ ተንደላቀህ ትኖር ነበር፡፡ ዕድለ-ቢስ ነህ፣ ተረግመሃል” ሲሉ ዘበቱበት፡፡
ሽማግሌው ረጋ ብሎ “እስቲ ቸኩላችሁ አትናገሩ፣ ‘ፈረሱ በጋጣው ውስጥ የለም’ ብቻ በሉ፣ ተረግሜ ይሁን አይሁን በምን አውቃለሁ? እናንተስ እንዴት ታውቃላችሁ?” አላቸው፡፡  ሰዎቹ አልተቀበሉትም፣ “ልታሞኘን አትችልም” ብለውት ሄዱ፡፡
ከአሥራ አምስት ቀናት በኋላ ፈረሱ ተመለሰ፡፡ አልተሠረቀም፣ ወደ ጫካው ነበር የሄደው፡፡ ሲመለስ ግን ብቻውን አልተመለሰም፣ ደርዘን ያህል የዱር ፈረሶች አብረውት ነበሩ፡፡ በዚህ ጊዜ የመንደሩ ሰዎች እንደገና ተሰብስበው ወደ ሽማግሌው ዛፍ ቆራጭ መጡና “አንተ ልክ ነበርክ፣ እኛ ነን የተሳሳትነው፡፡ እርግማን ነው ያልነው ለካ ምርቃት ነበር፡፡ እባክህን ይቅር በለን” አሉት፡፡
ሽማግሌው ግን እንዲህ አላቸው፣ “አሁንም ርቃችሁ እየሄዳችሁ ነው፡፡ ‘ፈረሱ ተመለሰ፣ ደርዘን የሚሆኑ ፈረሶችም አብረውት መጥተዋል’ ብቻ በሉ፡፡ ይህ ምርቃት ይሁን እርግማን እንዴት ልታውቁ ይቻላችኋል? የመጽሐፉን አንድ ገጽ ብቻ አንብባችሁ ስለሙሉው መጽሐፍ እንዴት መፍረድ ትችላላችሁ?”
“ሽማግሌው ልክ ሊሆን ይችላል” አሉ ሰዎቹ እርስ በርሳቸው፡፡ ውስጣቸው ግን እነርሱ ትክክል እንደሆኑ ይነግራቸዋል፡፡ ከዚያም ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡
ሽማግሌው ብቸኛ ወንድ ልጅ ነበረው፡፡ ይኸው ልጁ የዱር ፈረሶቹን መግራት ጀመረ፡፡ አንድ ቀን አንደኛውን ፈረስ እየገራው እያለ ፈረሱ ይጥለውና ሁለቱም እግሮቹ ይሰበራሉ፡፡ የመንደሩ ሰዎች የደረሰውን አደጋ ሰምተው ሊጠይቁትና አባትየውን ሊያጽናኑት ወደቤቱ መጡ፡፡
“አንተ ልክ ነበርክ፡፡ በእነዚህ የተረገሙ ፈረሶች ምክንያት ይኸው ልጅህ እግሮቹ ተሰበሩ፡፡ ከእንግዲህ ማን ይረዳሃል? በጣም ተጎዳህ” አሉት ጎረቤቶቹ ልጁን ከጠየቁ በኋላ፡፡
ሽማግሌው ተበሳጨ፡፡ “እናንተ ሰዎች! በፍርድ ተለክፋችኋል እንዴ? ርቃችሁ አትሂዱ፡፡ ‘ልጁ እግሮቹ ተሰበሩ’ ብቻ በሉ፡፡ ይህ እርግማን ይሁን ምርቃት ማን ያውቃል? የምናውቀው ጫፉን ብቻ ነው፣ ሙሉውን ታሪክ አናውቅም” አላቸው፡፡
ይህ ከሆነ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ አገሪቱ ከጎረቤት አገር ጋር ጦርነት ውስጥ ገባች፡፡ የመንደሯ ወጣቶች በሙሉ ለዘመቻ ሲጠሩ፣ እግሮቹ የተሰበሩት የሽማግሌው ልጅ ብቻ ቀረ፡፡ ልጆቻቸው የዘመቱባቸው የመንደሯ ሰዎች እያለቀሱ ወደሽማግሌው ዛፍ ቆራጭ ዘንድ መጡና “አንተ አሁንም ልክ ነህ፡፡ በልጅህ ላይ የደረሰው አደጋ በረከት ነው፡፡ ከዘመቻው ቀርቶ ካንተ ጋር ነው ያለው፡፡ እኛ ግን ልጆቻችንን መልሰን እናያቸው እንደሆነ አናውቅም” አሉት፡፡
“ከእናንተ ጋር መነጋገር አስቸጋሪ ነው” አላቸው ሽማግሌው፡፡ “አዎ፣ የእናንተ ልጆች ወደጦርነቱ ሄደዋል፣ የእኔው ግን አልሄደም፡፡ ይህ በረከት ይሁን እርግማን ማን ማወቅ ይችላል? ጫፍ ብቻ ይዛችሁ ስለምን ትፈርዳላችሁ?” አላቸው አስከትሎ፡፡
የእኛ የኢትዮጵያዊያን ነገር እንደዚህ ነው፡፡
ለማመስገን ቸኩለን፣ ለመተቸት ቸኩለን፣ ለውዳሴ ቸኩለን፣ ለስድብ ቸኩለን፣ ለምርቃት ቸኩለን፣ ለእርግማን ቸኩለን፣… ለሁሉ ነገር ቸኩለን እንዴት እንለወጣለን? በግማሽ ሰምተን/አንብበን በሙሉ እየፈረድን እንዴት  እንታደሳለን? እንደሽማግሌው ያለ አስተዋይ ሰው የተናገረው ነገር እውነት ሲሆን “አንተ ልክ ነበርክ፣ እኛ ነበርን የተሳሳትነው” እያልን ነገር በመደጋገም፣ ነገ ደግሞ ተመልሰን ያንኑ እያደረግን ወደምንመኘው ብሩህ ነገ እንዴት መድረስ እንችላለን?

ለፍርድ አንቸኩል!

Friday, September 21, 2018

ስድብ አረም ይሆናል እንጂ አያርምም!

ከዛሬ አራት ዓመት ከአሥር ወር በፊት “ኧረ ጎበዝ ምን ነካን?!” በሚል ርዕስ አንድ ጽሑፍ ጽፌ ነበር (http://asnakesinesibhat.blogspot.com/2013/11/)፡፡ የጽሑፉ ሐሳብ በወቅቱ ቴዲ አፍሮን አስመልክቶ በማኅበራዊ ሚዲያው ላይ ይሰነዘሩ የነበሩ ዘለፋዎችና መሠረተ-ቢስ ትችቶችን መቃወምና መልስ መስጠት፣ እንዲሁም መምከር ነበር፡፡ ዛሬስ? የተለወጠ ነገር አለ?
እንደእኔ ዕይታ ከሆነ፣ የተለወጠ ነገር የለም፡፡ ካለም የባሰበት እንጂ የተሻለ አይደለም፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያው ለሁሉም አንደበት ስለሰጠና ማንም የመሰለውን መጻፍ ስለሚችል፣ መልካም ሐሳብ ከሚጽፈው ባልተናነሰ ክፉና ጠማማ ሐሳብ የሚቸከችከውም ቁጥሩ የጨመረ ይመስለኛል፡፡
እውነት ለመናገር፣ የአንዳንዶች ድድብና ከማናደድም አልፎ ያስቃል፡፡ ሰው መልካም ነገር ሲያደርግ ማመስገኑ ቢቀር ያለምንም ምክንያት መሳደብና መዝለፍ “አዋቂ” ከሚባለው ሰው የማይጠበቅ፣ ሕፃንነትም ያልሆነ፣ ደመ-ነፍሳዊ የሆኑት እንስሳት እንኳን የማያደርጉት ስም-አልባ ባሕርይ ስለሆነ፣ በግርምት የሚያስቅም ነው፡፡
ይህንን ሁሉ እንድል ያደረገኝ ከቴዲ አፍሮ የበጎ አድራጎት ሥራ ጋር ተያይዞ በማኅበራዊ ሚዲያው ላይ አንዳንድ ሰዎች ያሠፈሯቸው አስተያየቶች የፈጠሩብኝ ሀዘንና ቅሬታ ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፤ በትናንትናው ዕለት ቴዲ አፍሮ ከቡራዩና አካባቢዋ ለተፈናቀሉ ወገኖች የአንድ ሚሊየን ብር እርዳታ ሰጠ፣ ይህንን ተከትሎም በማኅበራዊ ሚዲያው የተለያዩ አስተያየቶች ተሰጡ፡፡ አብዛኛዎቹ አስተያየቶች የአድናቆትና የምስጋና ሲሆኑ፣ የተወሰኑት ደግሞ ትችት፣ ሽሙጥ እና አለፍ ሲልም ዘለፋን ያዘሉ ነበሩ፡፡
እስቲ አሁን፣ ሰው ካለው ላይ ቀንሶ ለተጎዳ ወገኑ መቋቋሚያ ቢሰጥ ነውሩ ምንድን ነው? የአንዳንዶቹ ትችት “ለምን ሰጠ?” ዓይነት ተራ ምቀኝነት ይመስላል፡፡ የሌሎቹ ከሁነቱ ጋር ጨርሶ የማይገናኝ ሀሳብ ይዘው አራምባና ቆቦ ይረግጣሉ፡፡ ያሳፍራል!
ላለፉት አሥርት ዓመታት ቴዲ አፍሮ በሙያዊ ሥራውና በግለሰባዊ ማንነቱ፣ እንዲሁም በሚያደርጋቸው ተግባራት ምስጋናንም ሆነ ትችትን ሲያስተናግድ ኖሯል፡፡ መመስገኑ መልካም ነው፣ መተቸቱም በመልካም ከሆነ ክፋት የለውም፡፡ የሚያሳዝነው ግን አብዛኛው ትችትና ወቀሳ ከክፉ አዕምሮ የሚመነጭ ማሰናከያ መሆኑ ነው፡፡
ሦስት መስመር የቀበሌ ማመልከቻ አስተካክሎ መጻፍ የማይችለው ሁሉ የበሰለ ሀሳብን አጣፍጦ በበሰለ ግጥምና በውብ ዜማ የሚያቀርበውን ባለሙያ “መሃይም” ብሎ ይሳደባል፣ “አዝማሪ” ማለት “አመስጋኝ” ማለት መሆኑን የማያውቅ ተቺ ሙያውን መስደቢያ ሊያደርግ ይሞክራል፣ ከሚኖርበት ሠፈር አልፎ የማይታወቀው ሁሉ በሙያው ራሱንና አገሩን ያስጠራውን ሰው ስም-አልባ ሊያደርግ ይጥራል፣ ቴዲ በሙዚቃው ውስጥ የተወሰኑ ብሔሮችን ስም ከጠራ “እከሌ የተባለውን ብሔር ያልጠራው ስለሚጠላው ነው” የሚል የሴራ ንድፈ-ሐሳብ ይዞ ዘረኛ ሊያደርገው ይከጅላል፣  በሙያው ካገኘው ሀብት ለአገርና ለወገን ድጋፍ ቢያደርግ “ዘርፎ ያመጣው ነው” ከማለት የማይመለስ ምቀኛ ምላሱን ይዘረጋል፣ ሌላው ቢቀር “እነእገሌ ሲቸገሩ ለምን አልረዳቸውም” እያለ በገንዘቡ ሊያዝ የሚቃጣው ከንቱም አለ፣…፡፡
ሌላም ወገን አለ፤ በ”አድናቂነት” ሽፋን ቀና ትችትን የሚደፈጥጥ፡፡ የቴዲን ሙዚቃዊ ሥራዎች በሙያዊ ዓይን በመቃኘት “እዚህ ላይ እንዲህ ዓይነት ችግር አለበት፣ እዚያ ላይ በዚህ ቢቀይረው” የሚል ቀና ሂስና አስተያየት የሚሰጡ ባለሙያዎችን “ቴዲን የነካ..” በሚል አጉል አድናቂነት አፈር ድሜ ለማብላት ታጥቆ የሚነሳ፡፡

ሁለቱም ወገን አይጠቅምም፡፡ ጽንፍ ይዞ በመውደድ ወይም በመጥላት ላይ ብቻ የሚንጠለጠል ስሜት ይገድላል እንጂ አያለማም፡፡ በተለይ ቴዲ አፍሮ መክሊቱን አውቆ በሚሠራቸው መልካም የሙያና የበጎ አድራጎት ሥራዎቹ የሚናደዱና ለስድብ የሚቸኩሉ ሰዎች ጤንነታቸው ያጠራጥራል፡፡ ቴዲን ለማሳያነት አነሳሁ እንጂ፣ በሙያቸው፣ በገንዘባቸው፣ በሀሳባቸውና በሌላም ነገራቸው ለኢትዮጵያ መልካም የሚሠሩ ዜጎችን ፌስቡክ ላይ ተጎልተው ለማዋረድ የሚተጉ ሰነፎችን ሁሉ ይመለከታል፡፡ በርካታ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ደግሞ፣ የአሁኑን የአገራችንን ለውጥ “እንደግፋለን” የሚሉ መሆናቸው ሌላው አስቂኝ ነገር ነው፡፡ ፍቅር፣ ይቅርታ፣ አንድነት እና መደመር ካለቅንነት ዕውን አይሆኑም፣ ካለሚዛናዊነት አይሳኩም፡፡ እነዚህን ሳይዙ፣ የጠሉትን በጸያፍ ስድብ ጭምር እያዋረዱ “መደመር” የለም፡፡ ስድብ አረም ይሆናል እንጂ አያርምም! 

Monday, September 17, 2018

ለውጥ፣ ለጸጥታ ኃይላችን!


አዲስ ዜና ሆኖ አይደለም፣ ግን መነገር ያለበት መራር እውነታ ስለሆነ ነው የማነሳው።
የትናንትናው የአዲስ አበባ የተቃውሞ ሰልፍ እና ውጤቱ የጸጥታ ኃይላችን ላለፉት 27 ዓመታት እንዴት ሲደራጅና ሲገነባ እንደቆየ እንደገና ያየንበት አሳዛኝ ክስተት ሆኖ አልፏል።ዛሬም የአድማ መበተኛ ዘዴያችን ጥይት ብቻ መሆኑ ያሳፍራል።
ይበልጥ የሚያሳዝነው፣ ሌላ የአድማ መበተኛ ሳናጣ ገዳይ ጥይት ለመተኮስ መቸኮላችን ነው። ለኢንጂነር ስመኘው ቀብር በወጣው ሕዝብና በፖሊስ መካከል "አልፋለሁ፣ አታልፍም" አለመግባባት የተነሳውን ግጭት ለማብረድ የተተኮሰው አስለቃሽ ጢስ አልቆ ነው ትናንትና በጥይት አምስት ሰው የተገደለው? ሰልፉ ወደቤተመንግሥት ስላመራ ብቻ የቤተመንግሥቱ ጠባቂ ወታደሮች ክላሻቸውን ወድረው ከሰልፈኛው ጋር መፋጠጥ ነበረባቸው? ከፌዴራል ፖሊስ ጋር ተቀናጅቶ ተቀባይነት ባለው የአድማ ብተና መንገድ ሁኔታውን ማብረድ ከባድ ነበር?
አልነበረም! ችግሩ፣ የጸጥታ ኃይሉ የሠለጠነው ለመደብደብና ለመግደል መሆኑ ነው።ባይሆንማ ኖሮ፣"ጥቃት ይቁም" ብለው አደባባይ የወጡ ዜጎች ላይ ጥይት ያለቦታው አይተኮስም ነበር። እንደሰማነው ከሆነ፣ ፌዴራል ፖሊስ የቅዳሜና እሁዱ ጥቃት እንደሚፈጸም መረጃ ደርሶት ነበር። በደረሰው መረጃ መሠረት ተገቢውን እርምጃ ባለመውሰዱ መጠየቅም፣ መቀጣትም የሚገባው እርሱ ነበር።
ምናልባት ይህንን ማለት ሰብዓዊ ላይሆን ይችላል፤ ግን መባሉ ግድ ነው። ትናንት አዲስ አበባ ላይ አምስት ወገኖቻችንን የገደሉት ጥይቶች የሚገቡት ለቡራዩዎቹ አረመኔዎች ነበር።ንጹሃንን ያልታደገ፣ ግን ንጹሃንን የሚገድል የጸጥታ ኃይል ይዘን ይህንን ለውጥ ዕውን ማድረግ መቻላችን አጠራጣሪ ነው።
እናም፣ ለውጥ ለጸጥታ ኃይላችንም በጣም ያስፈልገዋል!