Sunday, November 15, 2015

ሚዛናዊነት ሆይ! ከወዴት አለህ?

ባለፈው ዓርብ ምሽት በፈረንሳይ ዋና ከተማ ፓሪስ በሦስት ሥፍራዎች በተፈጸመው የተቀናጀ የሽብር ጥቃት እስካሁን ድረስ ባለው መረጃ መሠረት የ129 ሰዎች ሕይወት ሲጠፋ፣ 352 ሰዎች መቁሰላቸው የሰሞኑ ዐቢይ ዜና ሆኗል፡፡ ይህ አሳዛኝ ክስተት መላውን ዓለም አስደንግጧል፣ አሳዝኗልም፡፡ ጥቃቱን በማውገዝ የዓለም ማኅበረሰብ በተለያዩ መንገዶች ከጥቃቱ ሰለባዎችና ከፈረንሳይ ጎን መቆሙን እየገለጸ ይገኛል፡፡ የዚህ አካል በመሆንም ፌስቡክ ተጠቃሚዎቹ የገጽ መለያ ፎቶዋቸውን (profile picture) በፈረንሳይ ሰንደቅ ዓላማ ቀለማት በመሸፈን ሐዘናቸውን የሚገልጹበትን ዘዴ ከትናንት ጀምሮ ይፋ አድርጓል፡፡
በመሠረቱ ሽብርተኝነት በየትኛውም መነሾ ይምጣ፣ ምንም ዓይነት አመክንዮ ይሰጠው፣ ሊወገዝ የሚገባው እኩይ ድርጊት ነው፡፡ በየትኛውም የዓለም ክፍል የሚፈጸም የሽብር ድርጊት ሐዘኑና ሕመሙ የመላው ዓለም መሆኑ አይካድም፡፡ ከዚህ አንጻር ፌስቡክም ሆነ ሌሎች አካላት የፓሪሱን የሽብር ጥቃት ማውገዛቸውና ለተጎጂዎች ያላቸውን አጋርነት መግለጻቸው የሚደገፍ ነው፡፡ ነገር ግን፣ ይህ ሽብርተኝነትን የማውገዝ እንቅስቃሴ ”ለሁሉም በእኩል የሚደረግ ነው ወይ?” የሚለው ጥያቄ፣ ብዙ የሚያነጋግር ይመስለኛል፡፡
በዘመናችን በርካታ አገራት የሽብር ጥቃት ሰለባዎች ሆነዋል፡፡ ዓይነቱ ቢለያይም፣ በየአገራቱ በሚፈጸሙ የሽብር ጥቃቶች የንፁሃን ሕይወት መጥፋቱ ፣ በተለይ በዚህ ወቅት፣ በጣም እየበዛ መጥቷል፡፡  ከላይ እንደገለጽኩት፣ ሽብርተኝነት በየትኛውም መለኪያ ሊወገዝ ይገባዋል፡፡ ከአገር አገር የሚለያይ ደረጃ እየወጣለት ለአንደኛው አገር ማልቀስ፣ ለሌላኛው ደግሞ ጀርባ መስጠት አግባብ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ሽብርተኝነት፣ የትም ሆነ የት፣ ሽብርተኝነት ነውና፡፡
ከሁለት ሳምንታት በፊት በግብጽ የሲናይ በረሃ ላይ በአየር ላይ ፈንድቶ የተከሰከሰው የሩሲያ የመንገደኞች አውሮፕላን የአደጋ መነሾ በአውሮፕላኑ ውስጥ በሻንጣ ተደብቆ የገባ ቦንብ መሆኑ ተገልጾአል፡፡ በዚህም መነሻነት አውሮፕላኑ የሽብር ጥቃት ሰለባ እንደሆነ በስፋት ታምኗል፡፡ በተጨማሪም በአሁኑ ዘመን የዓለማችን ቁጥር አንድ አሸባሪ የሆነው አይሲል እና የግብጽ አጋሩ አውሮፕላኑን ማጋየታቸውን በይፋ ገልፀው ኃላፊነቱን ወስደዋል፡፡ በዚህ ጥቃት 224 ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል፣ ይህን ተከትሎ ግን ፌስቡክም ሆነ ሌሎች፣ እንዲሁም መላው ዓለም፣ ለፈረንሳይ ያዘኑትን ሐዘን ያህል ለሩሲያ ሐዘናቸውን አልገለጹም፡፡ በተለይ ፌስቡክ፣ ተጠቃሚዎቹ ፎቶዋቸውን በሩሲያ ሰንደቅ ዓላማ ቀለማት እንዲሸፍኑ ዕድሉን አልሰጠም፡፡ ለምን?
ይህን ጥያቄ የምጠይቀው ምክንያቱ የፖለቲካ ጎራ አሰላለፍ ልዩነት መሆኑ ጠፍቶኝ አይደለም፡፡ ይልቁን፣ ምዕራባዊያን የሐዘን መግለጫ የኢንተርኔት ገጽ ሲያዘጋጁልን፣ የሐዘናቸው ሚዛን-አልባነት ቢከነክነኝ ያነሳሁት ጥያቄ ነው፡፡ ከፈረንሳይ የበለጠ ቁጥር ያላቸው ዜጎቿን ያጣችውን ሩሲያን ”እግዜር ያጥናሽ” የምንልበት ዕድል ያልሰጠን ፌስቡክ ለፈረንሳይ ሐዘን፣ እንደሰፈር ዕድር ”ድንኳን ተካይ፣ ንፍሮ ቀቃይ” ልሁን ማለቱ በበኩሌ ሊዋጥልኝ አልቻለም፡፡ እንዲህ ያለው መንታ ሚዛን (double standard) የዓለማችንን ዋነኛ ስጋት ምክንያታዊ በሆነ ዕይታ እንዳናወግዝና እንዳንዋጋ እንቅፋት ይሆንብናል ብዬ አስባለሁ፡፡ እኛ ኢትዮጵያዊያንም፣ የሐዘኑ ተካፋይ ብንሆንም፣ እኛም በአይሲል ወገኖቻችንን በአሰቃቂ ሁኔታ ባጣን ጊዜ ሐዘናችንን ብቻችንን እንዳዘንን በማስታወስ፣ ይህንን የፌስቡክ የሐዘን መግለጫ መንገድ ተጠቅመን ሐዘናቸንን ስንገልጽ፣ ”ሚዛናዊነት ሆይ! ከወዴት አለህ?” ብለን መጠየቅ ይገባናል፡፡ 


Monday, October 12, 2015

ማሳሰቢያ፤ ለባለሙያዎች

ሰሞኑን የአውሮፓ የፊልም ፌስቲቫል በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡ ከመስከረም 21 እስከ ጥቅምት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. በጁቬንቱስ ክለብ፣ በአሊያንስ ኢትዮ-ፍራንሴዝ፣ በጎተ ኢንስትቲዩት፣ እና በብሪትሽ ካውንስል ከአሥራ ሰባት አገራት የተውጣጡ ፊልሞች ለዕይታ እየቀረቡ ይገኛሉ፡፡ በኢትዮጵያ ሲካሄድ ከሃያ አምስት ዓመታት ያላነሰ ጊዜን ያስቆጠረው ይህ ፌስቲቫል ከዓመት ዓመት የተመልካች ብዛቱ እየጨመረ ያለና ከከተማችን ዐበይት ጥበባዊ ክንውኖች መካከል አንዱ ለመሆን የበቃ ነው ማለት ይቻላል፡፡ እኔም ከአሥር ዓመታት በላይ በዘለቀው የዚህ ፌስቲቫል ታዳሚነቴ ብዙ ነገሮችን ለመማር የቻልኩበትና የምዝናናበትም መድረክ በመሆኑ በየዓመቱ በካሌንደሬ ውስጥ በቋሚነት ከምመዘግባቸው ፕሮግራሞች መካከል አንደኛው ነው፡፡ ዘንድሮም አብዛኞቹን ፊልሞች ተመልክቻለሁ፣ በዕውቀትም ሆነ በመዝናናት ጥሩ ጥቅም እያገኘሁበት እገኛለሁ፡፡
አሁን ላነሳው የፈለግሁት ሐሳብ በቀጥታ ፌስቲቫሉን የሚመለከት አይደለም፡፡ ሐሳቤ በአጠቃላይ በከተማችን የሚገኙ የተለያዩ ተቋማት በሚያዘጋጇቸው መድረኮች ላይ ያለንን ተሳትፎ፣ በተለይም በመድረኮቹ የሚነሳው ሐሳብ በቀጥታ የሚመለከታቸው ባለሙያዎች በመድረኮቹ ላይ ለመገኘት ያላቸውን ተነሳሽነት የሚጠይቅ ነው፡፡
ይህንን ሐሳብ ከላይ በጠቀስኩት የአውሮፓ ፊልም ፌስቲቫል አብሮኝ ከሚታደመውና ከፌስቲቫሉ ጋር ካስተዋወቀኝ ወዳጄ ጋር ስንወያይበት ነበር፡፡ አምና በተካሄደው መሰል ዝግጅት ላይ ካገኘሁት አንድ የፊልም ባለሙያ ጋርም በሰፊው ተነጋግረንበት ነበር፡፡ ከወዳጄ ጋር በዘንድሮው ፌስቲቫል ላይ እስከትናንትናው ምሽት ድረስ ያየናቸው የፊልምና የትወና ባለሙያዎች ሦስት ብቻ ናቸው (በአደባባይ  የማይታወቁ ሊኖሩ እንደሚችሉ ሳንረሳ)፡፡ በተለያዩ የቴአትር፣ የቴሌቪዥን፣ እና የፊልም ሥራዎች ላይ የምናውቃቸው አብዛኛዎቹ ባለሙያዎች ግን (ቢያንስ እኔ በተገኘሁባቸው ቀናት) የሉም፡፡ እንደውም እኔ ሳስበው፣ እነዚህ ባለሙያዎች ስለፌስቲቫሉ መኖር ጨርሰው የሚያውቁም  አይመስለኝም፡፡
እንደዚህ ዓይነቱ ነገር በሌሎችም ዘርፎች ላይ ብዙ ጊዜ ይገጥመኛል፡፡ እኔ ከዩኒቨርሲቲ ተማሪነት ጊዜዬ አንስቶ ባመቸኝ ጊዜ ሁሉ የማልገኝበት መድረክ የለም፤ የፓናል ውይይት፣ ሌክቸር፣ ኤግዚቢሽን፣ የመጽሐፍ ምረቃ፣ ፊልም፣ ሙዚቃ፣ ወዘተ፡፡ ርዕሰ-ጉዳዩ ተመለከተኝም አልተመለከተኝ፣ ዘርፌ ሆነ አልሆነ መገኘት ከቻልኩና ፍላጎቴ ከሆነ እታደማለሁ፡፡ ታዲያ የሚገርመኝ ነገር፣ የምገኝበት መድረክ ርዕሰ-ጉዳይ በቀጥታ ከሚመለከታቸው (ሥራቸው ከሆኑት) ሰዎች መካከል በመድረኩ ላይ የሚገኙት በጣት የሚቆጠሩት መሆናቸው ነው፡፡ በተለይ ደግሞ በዘርፋቸው ተተኪዎችን ማፍራት እንጀራቸው የሆኑ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን [አብዛኛዎቹ] አይገኙም፡፡
ባለሙያዎቹ በእነዚህ መድረኮች ስላለመገኘታቸው ቢጠየቁ የሚሰጧቸው የተለያዩ ምክንያቶች ይኖሯቸዋል ብዬ እገምታለሁ፡፡ አንዳንዶቹ መረጃ ባለማግኘት፣ ሌሎቹ ”ቢዚ በመሆን…፣”  የቀሩትም በሌሎች ምክንያቶች ”መገኘት አልቻልንም” ሊሉ ይችላሉ፡፡ ምናልባት ”ቢዚ” መሆን (በተለይ ማታ ለሚያስተምሩ መምህራን) ልቀበለው የምችለው ምክንያት ቢሆንም፣ ሌሎቹ ምክንያቶች ግን አያሳምኑኝም፡፡ ለምን ቢባል፣ መረጃ አለማግኘትም ሆነ መሰል ሰበቦች ለእኔ መነሻቸው ”ስንፍና” ስለሆነ፡፡
አንድ የተማረ ሰው ሙያውን አስመልክቶ ስለሚደረግ ስብሰባ፣ ውይይት፣ ወይም መሰል ክንውን ለማወቅ መረጃው ቢሮው ወይም ቤቱ ድረስ እስኪመጣለት መጠበቅ የለበትም፡፡ ”ምን አዲስ ነገር አለ?” ብሎ መጠየቅ፣ ሚዲያ መከታተል፣ በተለይም ደግሞ በዚህ የኢንተርኔት ዘመን መረጃውን ጎልጉሎ ማውጣት በቀላሉ ሊያደርጋቸው የሚችሉ ነገሮች ይመስሉኛል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቀለም-ቀመስ የሆነ ሰው ራሱን በተማረው ነገር ብቻ አጥሮ መቀመጥ አይገባውም ባይ ነኝ፡፡ የተለያዩ የሙያ ዘርፎች እርስ በርስ ሊደጋገፉ ይችላሉ፣ በትምህርት ቤት ከምናገኘው ሙያዊ ዕውቀት በተጨማሪ በውይይቶች የምናገኛቸው በርካታ ጠቃሚ ዕውቀቶችና መረጃዎች አሉ፣ ከእኛ ዕውቀትና ሙያ ውጭ ያሉ ሌሎች ዘርፎች አስደሳችና አመራማሪ ሊሆኑ ይችላሉ፣ ሌሎችም ብዙ ጠቀሜታዎች ከእነዚህ መድረኮች ይገኛሉ፡፡ ደግሞም እነዚህ መድረኮች ከሥራ በኋላ ማምሻውን ለድራፍት የምናወጣውን ወጪ የግማሹን ግማሽ እንኳን የማያስወጡ (በአብዛኛው ከ12 ሰዓት በኋላ የሚካሄዱና ከክፍያ ነፃ) በመሆናቸው ብዙ የምናተርፍባቸው ዕድሎች እንደሆኑም ማሰብ ያስፈልጋል፡፡

ለዚህ ሁሉ ግን ዋናው ፍላጎት ይመስለኛል፡፡ ለማወቅ የሚኖር ፍላጎት፣ ሁሉን አቀፍ ዕይታን ለማዳበር የሚኖር ፍላጎት፣ ጤናማ የዕረፍት ጊዜ ማሳለፊያ ለማግኘት የሚኖር ፍላጎት፡፡ በፍላጎት ብቻ ትምህርት ቤት ሳይገቡ ብዙ የሚያውቁ ሰዎች አንደኛው የዕውቀታቸው ምንጭ ዕውቀት የሚገኝባቸውን ቦታዎች አሳድደው በማግኘት መሳተፋቸው ነው፡፡ መማር የቻልን ሰዎች ደግሞ የበለጠው ዕድል በእጃችን ነውና ብንጠቀምበት ትርፋችን የበዛ ይሆናል፡፡ 

Sunday, August 30, 2015

ማሳሰቢያ፤ ለማስታወቂያ ሠሪዎች

በዚህ ሰሞን በሬዲዮና በቴሌቪዥን እየቀረበ ያለ አንድ ማስታወቂያ አለ፡፡የማስታወቂያው ባለቤት ብሔራዊ ሎተሪ ሲሆን፣ ጳጉሜን 6 ቀን የሚወጣውን ”እንቁጣጣሽ ሎተሪ”ን ለማስተዋወቅ የተሠራ ነው፡፡ በማስታወቂያው ላይ ባልና ሚስት በእንቁጣጣሽ ዕለት የአገር ባሕል ልብሳቸውን ለብሰው ድፎ ዳቦ ቆርሰው ለመብላት እየተዘጋጁ ሳለ ”አበባየሆሽ” የሚጨፍሩ ልጃገረዶች ወደቤታቸው መጥተው፡
”ሆ ብለን መጣን ሆ ብለን፤
ስድስት ሚሊየን ይዘን…፡፡”
እያሉ ሲያዜሙና ጥንዶቹም ድፎ ዳቦና ለሎተሪ መግዣ የሚሆን ገንዘብ ሰጥተው ሲሸኟቸው ያሳያል፡፡
የማስታወቂያው ዓላማ ለአዲስ ዓመት መግቢያና መቀበያ የተዘጋጀውን ሎተሪ ማስተዋወቅ እንደመሆኑ በዓል በዓል የሚሸት ትዕይንት መያዙ ብዙም ላያስገርም ይችላል፡፡ ነገር ግን የማስታወቂያው አዘጋጆች አንድ ትልቅ ነገር ረስተዋል፣ የጊዜ ቅደም-ተከተልን፡፡ ልብ በሉ! የሎተሪው ዕጣ የሚወጣው ጳጉሜን 6፣ የበዓል መስተንግዶውና አበባየሆሹ የሚደረገው ከዕጣው መውጫ (የእንቁጣጣሽ ዋዜማ) እና ከበዓሉ ቀናት በፊት፡፡
ለመሆኑ ከመቼ ወዲህ ነው አበባየሆሽ በነሐሴ የሆነው? በየትም አገር የበዓል አከባበር የበዓል ድግስ በዋዜማውም ሆነ አስቀድሞ ባለ ቀን አይበላም፣ አይጠጣም፡፡ የግድ ሎተሪውን ከበዓሉ ጋር ለማገጣጠም ሲባል ብቻ ነገሮችን ያለጊዜው ማምጣት አግባብ አይደለም፡፡ የዚህ ማስታወቂያ አዘጋጆች ጊዜ ወስደው ቢያስቡበት ኖሮ እንቁጣጣሽ ሎተሪን ከእንቁጣጣሽ ጋር የሚያያይዙ ብዙ ትዕይንቶችን መሥራት ይችሉ ነበር፡፡ ከዓመት በዓል ሸመታ ጋር፣ ከበዓል ስጦታ ጋር፣ ከዋዜማ ምሽት የእንኳን አደረሳችሁና የመልካም ምኞት ልውውጥ ጋር፣ ወዘተ ማገናኘት ይቻላል፡፡ ነገር ግን የይድረስ ይድረስ ሥራ ሆነና የማይመስል ማስታወቂያ ተሠራ፣ ብሔራዊ ሎተሪም ያለበቂ ግምገማ ”ይሁን” ብሎ አቀረበልን፡፡
ማስታወቂያ ግነትን እንጂ ውሸትን አይፈልግም፡፡ ከእውነታ ጋር የተጋጨ ማስታወቂያ ውሸት እንጂ ሌላ ምንም ስም የለውም፡፡ የማስታወቂያ አዘጋጆች ገንዘብን ብቻ እያያችሁ ያለዕውቀትና ያለጥንቃቄ የተሠራን እውነት ያልሆነ ድራማ ”ማስታወቂያ ” እያላችሁ እባካችሁ አትቀልዱብን፡፡ ባለማስታወቂያዎችም በግዴለሽነት የተሠራላችሁን ማስታወቂያ ሳትገመግሙ እያሳለፋችሁ ሥርዓት አታፍርሱ፡፡ ሚዲያዎችም ብትሆኑ ገና ለገና ”ሳንሱር ቀርቷል” ብላችሁ የመጣላችሁን ማስታወቂያ ሁሉ ሳትፈትሹ አትልቀቁ፡፡ የሚታዘብ ሕዝብ፣ የሚያድግና የሚማር ትውልድ አለና!

Wednesday, August 12, 2015

ቴሌቪዥን፣ ልጆችና ወላጆች- ፫

በክፍል ሁለት ጽሑፌ ቴሌቪዥንን አብዝቶና ያለምርጫ መመልከት በሕጻናትና ታዳጊዎች ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ አስመልክቶ ሳይንሳዊ ጥናቶች የደረሱበትን ድምዳሜ በአጭሩ ለመዳሰስ ሞክሬ ነበር፡፡ ጥናቱ ዕድሜያቸው ከ2 እስከ 11 ዓመት የሆናቸው ሕጻናት ከቴሌቪዥን ጋር ባላቸው ቆይታ ምን ዓይነት ተጽዕኖዎች እንደሚደርሱባቸው ያመለከተ ሲሆን አብዛኞቹ ተጽዕኖዎች አሉታዊ መሆናቸውን ከጥናቱ ውጤት ለማየት ተችሏል፡፡
ይህ ጥናትም ሆነ ሌሎች ጥናቶች በርከት ያሉ ጎጂ ተጽዕኖዎችን የዘረዘሩ ቢሆንም፣  ለኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ የሚቀርቡት ጉዳቶች ባለፈው ጽሑፍ ላይ ተጠቃለው የቀረቡት በመሆናቸው በዚሁ እናቁመውና በዚህኛው ጽሑፍ ለልጆቻችን ጤናማ የቴሌቪዥን ዕይታ የሚጠቅሙ የመፍትሄ ሐሳቦችን እንቃኛለን፡፡
መፍትሄው ምንድን ነው?
ሲንዲ ስሚዝ የተለያዩ ባለሙያዎችና ተቋማት ወላጆች የልጆቻቸውን ጤናማ የቴሌቪዥን ዕይታ ለማረጋገጥ ያግዟቸዋል በማለት ካስቀመጧቸው የመፍትሄ ሐሳቦች መካከል የተወሰኑትን እንደሚከተለው አቅርበዋቸዋል፡፡
1.    የቴሌቪዥን መመልከቻ ሰዓትን መወሰን፡- ሕጻናት እንደ ዕድሜያቸው የተለያየ የቴሌቪዥን መመልከቻ የሰዓት ገደብ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ በተለይ ዝቅተኛ ድሜ ላይ ያሉ ልጆች ለረጅም ሰዓት ቴሌቪዥን መመልከት አይገባቸውም፡፡ ስለዚህም፡-
 
ሀ. ከ2 ዓመት በታች፡- የአሜሪካ የሕጻናት ሕክምና ማኅበር (American Association of Pediatrics) እና በርካታ ኤክስፐርቶች ዕድሜያቸው ከሁለት ዓመት በታች የሆኑ ሕጻናት በጭራሽ ቴሌቪዥን መመልከት አይኖርባቸውም ሲሉ ይመክራሉ፡፡ ለዚህ ምክንያቱ የጨቅላ ሕጻናት አዕምሮ በፈጣን ሁኔታ የሚለዋወጡ ምስሎችና ንግግሮችን ለማስተናገድ በሚያስችል ደረጃ የተዋቀረ ባለመሆኑ ነው፡፡ ለዚህ የዕድሜ ክልል ተብለው የሚዘጋጁ ዲቪዲዎች ቢኖሩም እንኳ አንድ ሕጻን የግንኙነትና የተግባቦት ክህሎቱን ሊያዳብር የሚችለው ከሌሎች ጋር አብሮ በመሆኑ ብቻ ነው እንጂ በዲቪዲው ዕይታ ምክንያት አይደለም ይላሉ ባለሙያዎቹ፡፡
ለ. ከ2 እስከ 3 ዓመት፡- በብሪታኒያ የታወቁት የንግግርና የቋንቋ ቴራፒስት ዶ/ር ሳሊ ዋርድ በዚህ የዕድሜ ክልል ያሉ ሕጻናት የቴሌቪዥን መመልከቻ ጊዜ በቀን ለግማሽ ሰዓት ብቻ መሆን እንዳለበት ይመክራሉ፡፡
ሐ. ከ3 እስከ 5 ዓመት፡- እንደባለሙያዎቹ ለዚህ የዕድሜ ክልል በቀን ለአንድ ሰዓት ብቻ ቴሌቪዥን መመልከት በቂ ነው፡፡

2.   ቴሌቪዥንን በማይታይበት ጊዜ ማጥፋት፡- በቤታችሁ ውስጥ ቴሌቪዥን ተከፍቶ የሚመለከተው ሰው ከሌለ አጥፉት፡፡ ከቴሌቪዥኑ የሚወጣው ድምጽ ትኩረትን የሚሠርቅ ስለሆነ ልጆቻችሁ በሌሎች ጠቃሚ ነገሮች (ለምሳሌ የወላጆች ድምጽ) ላይ እንዳያተኩሩ ያደርጋቸዋል፡፡ በተለይ ከሰዎች ጋር የግንኙነት መዘግየት ችግር ላለባቸው ልጆች ይህ ጠቃሚ መፍትሄ ነው ይላሉ ባለሙያዋ፡፡

3.   ተስማሚ ፕሮግራሞችን መምረጥ፡- ልጆቻችሁ የሚወዷቸውን፣ ነገር ግን ለዕድሜና የዕድገት ደረጃቸው የሚመጥኑና የአዋቂ ይዘት(adult theme) የሌላቸውን ፕሮግራሞች እንዲመለከቱ ፍቀዱላቸው፡፡  በተለይ ልጆቻቸሁ በወደፊት ሕይወታቸው ውስጥ ከሚገጥሟቸው ተሞክሮዎች ጋር የተገናኙ ፕሮግራሞች ተመራጭ ናቸው፡፡

4.   ፕሮግራሞችን አብሮ መመልከትና መወያየት፡- በተቻላችሁ መጠን ከልጆቻችሁ ጋር የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን ለመመልከት ሞክሩ፡፡ በዚህ ጊዜ ታዲያ በፕሮግራሙ እየተደረገ ስላለው ነገር አብዝታችሁ ከልጆቻችሁ ጋር ተወያዩ፡፡ ሁልጊዜ አብራችሁ ለመመልከት ካልቻላችሁ የፕሮግራሙን ተስማሚነት አስቀድማችሁ አረጋግጡ፡፡ ለሕጻናት በሚቀርቡ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ውስጥ የተለመዱት ገጸ-ባሕርያት ተወዳጅ ቢሆኑም፣ አስፈሪ የሆኑትን ግን እንዳይመለከቱ ተጠንቀቁ፡፡
 
5.   አማራጮችን ማሰብ፡- ቴሌቪዥንን አብዝተው የሚመለከቱ ልጆች አልፎ አልፎ የንባብ ችሎታ ማነስ ችግር ያጋጥማቸዋል፡፡ ንባብ በልጆች የወደፊት የትምህርት ስኬት ላይ ወሳኝ ግብዓት በመሆኑ ልጆቻችሁን በትንሽነት ዕድሜያቸው ከመጻሕፍት ጋር እንዲላመዱ ጥረት አድርጉ፡፡ ልጆች በጨቅላነታቸው ጊዜ ማንኛውንም ዕቃ (አሻንጉሊቶቻቸውን ጨምሮ) የመወርወር፣ ከግድግዳ ጋር የማጋጨት፣ እና ለማኘክ የመሞከር ልምድ ስላላቸው በዚህ ዕድሜያቸው የምትገዙላቸው መጻሕፍት የጠንካራ ፕላስቲክ፣ የጨርቅ፣ ወይም የካርድቦርድ ሊሆኑ ይገባል፡፡ በዚህ መልኩ ከመጻሕፍት ጋር የተዋወቁ ሕጻናት ከወላጆቻቸው ጋር መጻሕፍትን አብሮ ማንበብን ይወዳሉ ሲሉ ባለሙያዋ ይመክራሉ፡፡
በአጠቃላይ ቴሌቪዥን መረጃ በመስጠት፣ በማስተማርና በማዝናናት በኩል ከፍ ያለ ሚና የሚጫወት የመገናኛ መሣሪያ ቢሆንም፣ በአግባቡ ካልተጠቀምንበት በልጆች አስተሳሰብ ላይ ከፍ ያለ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል መረዳት ይገባናል፡፡ ወላጆች ”ቴሌቪዥን ልጆቻችንን አበላሸ” ከሚል ጭፍን አመለካከት ወጥተው የወላጅነት ኃላፊነታቸውን በዕውቀት ላይ በተመሠረተ መንገድ ለመወጣት ቢሞክሩ ለልጆቻቸው ጤናማ አስተዳደግ መሠረት ስለሚጥሉ ከኃላፊነት መሸሹን ትተው የወላጅነት ግብራቸውን በአግባቡ መወጣት ይገባቸዋል እላለሁ፡፡

 

Thursday, August 6, 2015

ቴሌቪዥን፣ ልጆችና ወላጆች- ፪



ልጆች እና ቴሌቪዥንን አስመልክቶ ብዙ ስለማይነገርለት የወላጆች ኃላፊነት ሐሳቦችን መሰንዘር ጀምሬ ነበር፡፡ የአገራችን ወላጆች (ሁሉም ባይሆኑ አብዛኛው) በቴሌቪዥን የሚተላለፉ ፕሮግራሞች በልጆቻቸው ባሕሪና አስተሳሰብ ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ተጽዕኖ ጊዜ ወስደው ለማሰብ የሚጨነቁ አይመስለኝም፡፡ በቅርበት ከማውቃቸው ወላጆች መካከል በጣት የሚቆጠሩት ብቻ ናቸው የልጆቻቸውን የቴሌቪዥን ዕይታ የሚከታተሉና ጥንቃቄ የሚያደርጉት፡፡ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ ግድ ከማጣት በተጨማሪ አለማወቅም ነው ባይ ነኝ፡፡ ስለዚህ በዚህ ጽሑፌ ቴሌቪዥን በልጆች ላይ ስለሚያስከትለው ተጽዕኖ አንዳንድ ነጥቦችን ለማንሳት እሞክራለሁ፡፡
የሃያኛው መቶ ክፍለ-ዘመን የቴክኖሎጂ አብዮት ካፈራቸው ግኝቶች መካከል አንዱ የሆነው ቴሌቪዥን የዕድሜ ታላቁ የሆነው ሬዲዮ ለሰው ልጅ ከሰጠው መረጃን በድምጽ የማስተላለፍ ዕድል አንድ ደረጃ ከፍ ብሎ ምስልን በማከል በአካል ልንገኝባቸው በማንችላቸው ሥፍራዎች ሁሉ እንድንገኝ አስችሎናል፡፡ የመረጃ፣ የመማሪያና የመዝናኛ ምንጭ በመሆን የሚሰጠው ጠቀሜታ ከዘመን ዘመን እያደገና እየሰፋ በመሄድ ላይ ነው፡፡ በተለይ በአሁኑ ዘመን ከቴክኖሎጂው መዘመን ጋር ተያይዞ በእጃችን መዳፍ ላይ እስከመገኘት ድረስ ተራቋል፡፡
 በዚህ ዘመን የቴሌቪዥን ቻናሎች በጣም በዝተዋል፡፡ ብዛታቸው የፈጠረው ውድድር ቀደም ባለው ጊዜ ለተወሰኑ ሰዓታት ብቻ የነበረው የአየር ላይ ቆይታቸው ወደ ሃያ አራት ሰዓታት እንዲያድግ አድርጓል፡፡ ድሮ በባለዘንግ አንቴና በየቤታችን ይደርስ የነበረው የቴሌቪዥን ስርጭት ዛሬ በዲጂታል ስርጭት መቀበያ ሳህን (dish) እና የስርጭት መቀበያ መሣሪያ (decoder) እየመጣ ፣ ከሁለትና ሦስት ቻናሎች በላይ የማይታዩበት ጊዜ ቀርቶ በሺ የሚቆጠሩ ቻናሎችን በቴሌቪዥናችን መስኮት እየተመለከትን ነው፡፡ 
ይህ የቻናሎችና የፕሮግራሞቻቸው መብዛት አማራጭ በመስጠት በኩል ጥሩ የሚባል ጥቅም ይኖረዋል፡፡ ተመልካቾች እንደምርጫና ፍላጎታቸው የተለያዩ ቻናሎችን እያማረጡ መመልከት መቻላቸው መረጃ በማግኘት፣ በመማር፣ እና በመዝናናት ረገድ እርካታቸው ጨምሯል፡፡ በሌላ በኩል ግን በጊዜ ያልተገደበ እና ምርጫ-አልባ የሆነ ቴልቪዥን የመመልከት ልምድ ቀላል ያልሆነ ጉዳት ያስከትላል፡፡ ለረጅም ሰዓታት ቴሌቪዥን መመልከት የጤናና የሥነ-ልቡና ጉዳት እንደሚያስከትል በጥናት ተረጋግጧል፡፡ ይህ ጉዳት የቅርብ ክትትል በሚያስፈልጋቸው ሕፃናት ላይ ብቻ ሳይሆን በአዋቂዎችም ላይ የሚደርስ እንደሆነም ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ ሌላው የቴሌቪዥን ጉዳት የሚቀርቡት ፕሮግራሞች በተመልካቾችን አስተሳሰብና አመለካከት ላይ ሊያስከትሉ የሚችሉት አሉታዊ ተጽዕኖ ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጸው የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች በማስተማር፣ በማሳወቅ፣ መረጃ በመስጠት እና በማዝናናት ጠቀሜታቸው ከፍ ያለ ቢሆንም፣ በተለይ ደግና ክፉውን ለይቶ ለማወቅ ገና የሆኑት ሕጻናትና ታዳጊዎች ሊመለከቷቸው የሚገቡትን ፕሮግራሞች መርጦ እንዲመለከቱ ማድረግ ካልተቻለ በወደፊት ባሕሪያቸው ላይ አደገኛ የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ ያሳድራሉ፡፡
ጥናቶች ምን ይላሉ?
ለመሆኑ ቴሌቪዥን በሕጻናት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳድራል? ይህንን ጥያቄ ለመመለስ የተለያዩ ጥናቶች ተደርገዋል፡፡ እንደሚታወቀው በአገራችን እንኳን ይህንን ስለመሰለው ጉዳይ ቀርቶ በጣም አንገብጋቢ ስለሆኑ ጉዳዮቻችን ጥልቅ ጥናቶች አይደረጉም፣ ቢደረጉም እንኳን በተሟላ ሁኔታ ተደራጅተው ስለማይቀመጡ አግኝቶ መጠቀሙም አስቸጋሪ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ ጽሑፍ የምንመለከታቸው ጥናቶች ባደጉት አገሮች የተደረጉትን ይሆናል፡፡ የእነዚህ ጥናቶች ውጤት በተወሰነ መልኩ ከአገራችን ሁኔታ የሚለይባቸው መልኮች ቢኖሩትም፣ መነሻው ግን ተመሳሳይ ስለሆነ ከጥናቶቹ በመነሳት ለእኛ የሚሆነውን ድምዳሜ መውሰድ እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡
ቴሌቪዥን በሕጻናት እና ታዳጊዎች ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ አስመልክቶ የሚደረጉ ጥናቶች የትኩረት አቅጣጫዎቻቸው የተለያዩ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ፡-
1.       ልጆች በቀን ለምን የህል ሰዓታት ቴሌቪዥን ይመለከታሉ? እና
2.     በጨቅላነት ዕድሜ ቴሌቪዥን መመልከታቸው ምን ዓይነት ውጤት ያስከትላል? የሚሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ይሞከራል፡፡
ሲንዲ ስሚዝ የተባሉ የንግግር ነክ ሕመሞች ተመራማሪ (speech pathologist) “Television Watching: Practical Advice for Parents of Young Children” በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሑፍ ወላጆች ለምን ልጆቻቸው ቴሌቪዥን እንዲመለከቱ እንደሚያደርጉ ከልምዳቸው ተነስተው ሲያብራሩ ”አንዳንዶቹ ‘ልጄ የቴሌቪዥን ፕሮግራሙን ስለሚወደው፣’ ወይም ‘ ፊደላትን ስለሚማርበት’፣ ሌሎቹ ደግሞ ‘ልጄ ምግብ አማርጣ የምትመገብ ናት፤ ቴሌቪዥኑ ከተከፈተ ግን እየበላች እንደሆነ ስለማታስተውለው ያለምርጫ ትመገባለች፣’ ወይም ‘እኔ እራት ሳዘጋጅ ልጄ ቴሌቪዥን በማየት ስለምትጠመድ አትረብሸኝም’ የሚሉና መሰል ምክንያቶችን ይሰጣሉ” ይላሉ፡፡
ባለሙያዋ በጥናታቸው ቴሌቪዥን ዕድሜያቸው ከ2 እስከ 11 ዓመት ድረስ በሆኑ ሕጻናትና ታዳጊዎች ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ ተመልክተዋል፡፡ የጥናታቸው ትኩረት ሕጻናትና ታዳጊዎች በቀን ውስጥ ለስንት ሰዓታት ቴሌቪዥን እንደሚመለከቱ የሚፈትሽ ሲሆን፣ በተገኘው ውጤት መሠረት በዩናይትድ ስቴትስ አንድ ልጅ በአማካይ በቀን ከ4 ሰዓታት በላይ ቴሌቪዥን የሚመለከት ሲሆን፣ በካናዳ እና አውስትራሊያ በቀን ከ2 ሰዓታት በላይ፣ እንዲሁም በዩናይትድ ኪንግደም ከ2 ሰዓት ተኩል በላይ ልጆች ቴሌቪዥን ይመለከታሉ፡፡ ከዚህ በመነሳት ”አንድ ልጅ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲያጠናቅቅ በክፍል ውስጥ ካሳለፈው ጊዜ ይልቅ በቴሌቪዥን ፊት ተቀምጦ ያሳለፈው ጊዜ ይበልጣል” ይላል ጥናቱ፡፡
ይህ የልጆች የቴሌቪዥን ልምድ ታዲያ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ባይ ናቸው ሲንዲ ስሚዝ፡፡ ጉዳቶቹ በሦስት ዋና ዋና ክፍሎች ተመድበዋል፡፡
1.      አካላዊ ጤና፡- በምዕራባዊያን አገሮች ለሕጻናት ውፍረት በዋነኛነት ምክንያት ተደርገው ከሚወሰዱት ነገሮች መካከል አንዱ ልጆች ቴሌቪዥን፣ ቪዲዮና ዲቪዲ ለመመልከት፣ እንዲሁም የኮምፒዩተር ጌም ለመጫወት ሲሉ በርካታ ሰዓታትን ተቀምጠው ማሳለፋቸው ነው (ይህ ልምድ ወደ አገራችንም በአሁኑ ጊዜ እየመጣ መሆኑን ልብ ይሏል)፡፡ በዚህም የተነሳ የልጆች የአካል እንቅስቃሴ ልምድ ቀላል በማይባል ደረጃ እየቀነሰ ይገኛል፡፡
2.     ሥነ-ባሕሪያዊ ጤና፡- እንደ ባለሙያዋ ገለጻ፣ አንዳንድ ለሕጻናት ተብለው የሚዘጋጁ ፕሮግራሞች በአማካይ በሰዓት 20 የሚደርሱ የግጭት/ረብሻ ትዕይንቶችን የያዙ ናቸው፡፡ እነዚህ ትዕይንቶች በካርቱን ፊልሞች ላይ ከሚታየው የገጸ-ባሕርያት የእርስ በርስ መጋጨት አንስቶ በእውነተኛ ገጸ-ባሕርያት ከሚተወኑ የረብሻ (violence) ድርጊቶች ድረስ ይዘልቃሉ፡፡ አንዳንድ ባለሙያዎች ለረዥም ጊዜ የሚዘልቅ የሕጻናትና ታዳጊዎች የቴሌቪዥን ዕይታ ድርጊቶችን መሞከር፣ ፍርሃትን፣ እና ችግሮችን በኃይልና በጉልበት የመፍታት ዝንባሌን ያዳብራሉ ሲሉ ይከራከራሉ፡፡
3.     ቋንቋ እና አጠቃላይ ትምህርት፡- ይህንን ክፍል አስመልክቶ በርካታ ጥናቶች የተደረጉ ሲሆን፣ ውጤታቸው የተለያዩ ቢሆንም በአጠቃላይ ግን ”ዜናው ጥሩ አይደለም” ይላል የስሚዝ ጽሑፍ፡፡ እንደነዚህ ጥናቶች ከሆነ ለማስተማሪያ ተብለው የሚዘጋጁት ፕሮግራሞች ሳይቀሩ በጨቅላ ሕጻናት የቋንቋ ትምህርት ብቃት ላይ መቀነስን አስከትለዋል፡፡
(ይቀጥላል)


Tuesday, July 21, 2015

ቴሌቪዥን፣ ልጆችና ወላጆች- ፩


ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በብዛት ከምንሰማቸው ጉዳዮች መካከል ”ፊልም፣ ቴሌቪዥን፣ እና ሕጻናት” አንደኛው ነው፡፡ የዚህ ጉዳይ ዋነኛ መነሻ በቴሌቪዥን የሚተላለፉ ፕሮግራሞች እና ፊልሞች በሕጻናት እና ታዳጊዎች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳደራቸው ይመስለኛል፡፡ ወቅቱ ክረምት ነውና ሕጻናት እና ታዳጊዎች ከእነዚህ ፊልሞች እና ፕሮግራሞች ጋር ሰፋ ያለ ጊዜ ማሳለፋቸው (በአብዛኛው ካለወላጅ እና አሳዳጊ ክትትል) አሳሳቢነቱ አያጠያይቅም፡፡
መወያየቱ፣ መመካከሩ፣ እና መፍትሄ መፈለጉ የሚደገፍ ነው፤ ሆኖም የውይይቱና የክርክሩ ተሳታፊዎች ብዙውን ጊዜ ሲያነሱት የማልሰማው አንድ ጉዳይ ቢኖር የወላጅ/አሳዳጊ ኃላፊነት ነው፡፡ ወላጆችና አሳዳጊዎች ልጆቻቸው ስለሚመለከቷቸው የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችና ፊልሞች ምን ያህል ያውቃሉ?  የሚመለከቱትን ፕሮግራም እንዴት መቆጣጠር ይችላሉ? እነዚህንና መሰል ጥያቄዎችን አንስቶ የሚወያይና የሚያወያይ፣ የሚያጠናና የሚመራመር አካል (ባለሙያ ወይም ተቋም) እስካሁን ድረስ አላጋጠመኝም፡፡ በአብዛኛው ተወቃሽ ተደርገው የሚነሱት የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ናቸው፡፡ ስለወላጆችና አሳዳጊዎች ድርሻ ግን ምንም ነገር ሲነገር አልሰማሁም፣ የተጻፈም ነገር እስካሁን ድረስ አላገኘሁም፡፡
ስለዚህ ጉዳይ ማሰብ ከጀመርኩ ከአሥር ዓመታት በላይ አልፏል፣ ይህ ጽሑፍ ከተጀመረ ደግሞ ሁለት ዓመት ሊሆን ነው፡፡ ነገር ግን ርዕሰ-ጉዳዩ ሰፊ ከመሆኑ አንጻር ጊዜ ወስዶ ማሰብ ስላስፈለገኝና መጠነኛ ስንፍናም ተጨምሮበት ጽሑፉ እስካሁን ድረስ ከአንድ አንቀጽ በላይ ሳይሄድ ቆይቷል፡፡ አሁን ላይ እንደአዲስ ይህንን ጉዳይ እንድመለስበት ያደረገኝ በልጆች አስተዳደግ ላይ በቅርባችን የማያቸው ነገሮች የተለያዩ ጥያቄዎችን የሚያስነሱ ሆነው ስላገኘኋቸው ነው፡፡
ከላይ እንደጠቀስኩት ”ቴሌቪዥን፣ ልጆች፣ እና የወላጅ ኃላፊነት” ስለሚለው ጉዳይ ማሰብ ከጀመርኩ ቆይቷል (በትክክል ከአሥራ ሁለት ዓመታት በፊት ነው)፡፡ የዛሬ አሥራ አምስት ዓመት ገደማ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አማካይነት በአገር ውስጥ ይተላለፍ የነበረውን ”ቲቪ አፍሪካ” የተባለ ቻናል ታስታውሱታላችሁ፡፡ በወቅቱ ይህ ቻናል ለብዙ ተመልካቾች የመረጃና የመዝናኛ አማራጭ ሆኖ በመቅረቡ ተወዳጅነትን ለማትረፍ ጊዜ አልፈጀበትም፡፡ የተወዳጅነቱን ያህል ብዙ ትችቶችንም አስተናግዷል፡፡ ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ሰዎች ”ቲቪ አፍሪካ ልጆቻችንን እያበላሸ ነው” በማለት በተደጋጋሚ ሲወቅሱት ይሰማ ነበር- በጊዜው፡፡
ከእነዚህ ትችቶች መካከል ይበልጥ ትኩረቴን የሳበውንና ስለወላጅ ኃላፊነት እንዳስብ ያደረገኝን ሐሳብ የሰማሁት በ1995 ዓ.ም. ነበር፡፡ በወቅቱ በአንድ ስብሰባ ላይ አንድ ዕውቅ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የትውልዱን ሥነ-ምግባር አስመልክተው  ሲናገሩ ”አኔ እኮ ዛሬ ልጆቼን አላሳድግም፣ ልጆቼን የሚያሳድግልኝ ቲቪ አፍሪካ ነው” ብለው ነበር፡፡ ይህ አባባል የስብሰባውን ተሳታፊዎች ፈገግ አሰኝቶ ነበር፣ እኔንም አስቆኛል፣ ከሳቁ በኋላ ግን ቀደም ብሎ ከሰማኋቸው ትችቶችና ወቀሳዎች ጋር ተዳምሮ ነገሩ ከነከነኝ፡፡ ”የቴሌቪዥናቸውን አንቴናና የቲቪ አፍሪካን ፍሪኩዌንሲ አስተካክለው ቤታቸው ያስገቡት እራሳቸው ወላጆች ሆነው ሳለ ቻናሉን ለምን ይተቻሉ? ስለሚተላለፉት ፕሮግራሞች የሚሰጠውን ማሳሰቢያስ ለምን አይከታተሉም?” ብዬም ጠየቅሁ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የቲቪ አፍሪካ ፕሮግራሞች ይዘትና የስርጭት መርሐ-ግብር ምን እንደሚመስል ማወቅ ስለፈለግሁ የቲቪ አፍሪካን ድረ-ገጽ ጎበኘሁ፡፡  
በኢቲቪ-2 የሚተላለፈው የቲቪ አፍሪካ ስርጭት ከቀኑ 11 ሰዓት እስከ እኩለ-ሌሊት ድረስ የሚዘልቅ ቢሆንም፣ ቲቪ አፍሪካ ግን ለ24 ሰዓታት የተለያዩ ፕሮግራሞችን (ዜና፣ ድራማ፣ ሶፕ ኦፔራ፣ ፊልም፣ ሙዚቃ፣…) የሚያቀርብ ነጻ ቻናል መሆኑን ከድረ-ገጹ ላይ ለመረዳት ቻልኩ፡፡ በድረ-ገጹ ላይ የተቀመጠው የፕሮግራሞች ዝርዝር የእያንዳንዱን ፕሮግራም ዓይነትና ይዘት፣ እንዲሁም የተመልካቾች የዕድሜ ገደብ የሚገልጽ አጭር መግለጫ የያዘ ነው፡፡ በነገራችን ላይ የፕሮግራሞች የዕድሜ ገደብ መግለጫ በተለይ ፊልሞችና ድራማዎች በቴሌቪዥን መቅረብ ከመጀመራቸው በፊት በግልጽ ቋንቋ ለተመልካቾች ይገለጽ ነበር፡፡
ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ የወላጆችን ኃላፊነት አስመልክቶ ማሰብ የጀመርኩት፡፡ የቴሌቪዥን ቻናሉ ”የማስተላልፈው ፕሮግራም ከዚህ ዕድሜ በላይ ላሉ ተመልካቾች የሚሆን ነው” ብሎ ካሳወቀ፣ ቀሪው ኃላፊነት የወላጅ፣ የቤተሰብ፣ የአሳዳጊ ወይም የሞግዚት ነው፡፡ ይህንን ማድረግ የማይችሉ ወላጅና ቤተሰቦች፣ ቻናሉን ጥፋተኛ አድርገው ለመውቀስ የሚያስችላቸው ምንም ዓይነት ምክንያት አለ ብዬ አላምንም፡፡ ሥራቸውን አልሰሩማ!      


(ይቀጥላል)                                              

Sunday, July 12, 2015

ኃላፊነትን አለመውሰድ- አደገኛው ገዳይ!

ባለፈው ዓርብ ሐምሌ 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የሸገር ኤፍ.ኤም. 102.1 ”የዓርብ ልዩ ወሬዎች” ላይ ከቀረቡት ዜናዎች መካከል አንዱ ታላላቅ የአዲስ አበባ ሆቴሎች የኢንተርኔት አገልግሎት እየተቋረጠባቸው መቸገራቸውን የሚያትት ነበር፡፡ በተለይም ከሰኞ ሐምሌ 6 ቀን ጀምሮ ለአሥር ቀናት ያህል በከተማዋ በሚስተናገደው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ የመጡ የአንዲት አፍሪካዊት አገር ፕሬዚዳንት ባረፉበት ሆቴል የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ የተነሳ ከሹሞቻቸው ጋር መገናኘት አለመቻላቸውን የሆቴሉ ሥራ አስኪያጅ በእፍረት መግለጻቸው የወሬው መነሻ ነበር፡፡ በዘገባው ላይ የሆቴሎች ማኅበር ምክትል ፕሬዚዳንት የሆኑት የኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል ዋና ሥራ አስኪያጅ የችግሩን ስፋትና የሚመለከታቸው አካላት ተገቢ ምላሽ ለመስጠት ዳተኛ መሆናቸውን እርሳቸው በሚያስተዳድሩት ሆቴል የደረሰውን ችግር በማሳያነት አቅርበው በምሬት ሲናገሩም ተደምጠዋል፡፡
መቼም በእኛ አገር አንድ ችግር ሲያጋጥም ለችግሩ ፈጣን ምላሽ ማግኘት (በተለይ አሁን አሁን) ብርቅ እየሆነብን ነው፡፡ ይበልጥ የሚያስገርመው ነገር ደግሞ ችግሩን እንዲፈታ የሚጠበቀው አካል ለችግሩ መፈጠር ወይም ለመፍትሄው በቶሎ አለመምጣት የሚደረድረው ሰበብና ምክንያት ዓይነት ነው፡፡ ስለተፈጠረው ችግር መንስኤውን አጣርቶ ተገቢውን ምላሽ መስጠትና ለችግሩም መፈጠር ይቅርታ መጠየቅን የማይደፍሩ አገልግሎት ሰጪዎች በዝተዋል፡፡ እንዲያውም የችግሩን መነሻ ወደሌላ አካል ማላከክ ይቀናቸዋል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጥ ላይ አገልግሎት ሰጪው የሰጠው ምላሽም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡
ይህ ዜና በቀረበ በማግሥቱ (ቅዳሜ ሐምሌ 4 ቀን) ኢትዮ ቴሌኮም በሰጠው ምላሽ በኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል የተፈጠረው የኢንተርኔት መቋረጥ በኤሌክትሪክ ኃይል መጥፋት የተፈጠረ መሆኑንና የሆቴሉ ጄኔሬተር በራሱ አለመነሳቱን ባለሙያዎቹ አረጋግጠው ጄኔሬተሩ ሲስተካከል ኢንተርኔቱም ሥራውን መቀጠሉን አስረድቷል፡፡ አያይዞም በአዲስ አበባ ከሚገኙ ባለስም ሆቴሎች መካከል አብዛኞቹ የኢንተርኔት አግልግሎት እንደሌላቸው በጥናት በመረጋገጡ እንዲያስገቡ በተገለጸላቸው መሠረት አራቱ ብቻ እስካሁን ድረስ ማስገባታቸውን በመግለጽ ችግሩ የሆቴሎቹ እንደሆነ ለማሳየት ሞክሯል፡፡
የኢትዮ ቴሌኮም ምላሽ እኔን ፈጽሞ አላሳመነኝም፡፡ እስቲ አስቡት! ኢንተርኮንቲኔንታልን የሚያክል ትልቅ ሆቴል ኤሌክትሪክ ሲቋረጥበት ሳያውቅ ሲቀር፡፡ መብራቶች ሲጠፉ፣ ሊፍቶች ሥራ ሲያቆሙ፣ ኤሌክትሪክ ጠፍቶ ጄኔሬተሩ እንዳልተነሳ ሲያይ ጄኔሬተሩን የማይፈትሽ የሆቴል አስተዳደር አለ ብሎ ለማመን ያስቸግራል፡፡ እንኳን ሆቴልን ያህል ተቋም በየቤታችን የኤሌክትሪክ አቅርቦት ሲቋረጥ ቀድመን የምናየው ቆጣሪውን ነው፡፡ ምናልባት ከቆጣሪው ጠፍቶ እንደሆነ ለማረጋገጥ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኢንተርኔት ያለኤሌክትሪክ እንደማይሠራ ማንም የኢንተርኔት ተጠቃሚ የሚስተው አይመስለኝም፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም ሆቴሉ ይህንን ሁሉ ”አያውቅም ነበር” እያለን ነው፡፡ እንዲያውም ”ችግሩን እኔ ስለደረስኩበት ልመሰገን እንጂ ልወቀስ አይገባኝም” ዓይነት ምላሽ ይመስላል የሰጠው፡፡
እኔ እስከማውቀው ድረስ የገመድ-አልባ ኢንተርኔት አገልግሎት (wi-fi service) በሚቋረጥበት ጊዜ መልሶ ለማስጀመር የሚደረገው የኢንተርኔት ማገናኛ መሣሪያውን (router) አጥፍቶ እንደገና ማብራት ነው፡፡ ሆቴሉ መብራት ጠፍቶበት እንደገና ሲመጣ ይህንን ማድረግ እንዳለበት አያውቅም ለማለት ይከብደኛል፡፡ ከሥራ አስኪያጁ ገለጻ እንደተረዳሁት ችግሩ ከአንድ ቀን በላይ የቆየ እንደሆነ ነው፡፡ ታዲያ ይህንን ችግር እንዴት አድርጎ ነው ከኤሌክትሪክ መቋረጥ ጋር ብቻ ሊያያዝ የሚችለው?
ጉዳዩ ቴክኒካዊ ስለሆነ ምናልባት እኔን ያልገባኝ ሙያዊ ነገር ካለ እታረማለሁ፡፡ ነገር ግን የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጥ በትልልቅ ሆቴሎች ብቻ ሳይሆን የዋይ-ፋይ አገልግሎት በሚሰጥባቸው አነስተኛ ካፌዎች እና ቢሮዎችም ጭምር በዚህ ሰሞን እያጋጠመ ያለ ችግር ነው፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ምላሽ ይህንን ሁሉን አቀፍ ችግር ከግምት አስገብቶ የተሰጠ አይደለም፡፡ ከላይ እንደጠቀስኩት ኩባንያው ችግሩን ወደሌላ አካል የመግፋት ዓይነት አካሄድ ተከትሏል ባይ ነኝ፡፡ በሌላ አነጋገር ከተጠያቂነት ሽሽት ነው፡፡

መቼ ይሆን ስህተትንና ጥፋትን አምኖ ኃላፊነትን መውሰድ የምንለምደው? እርግጥ ነው! በግለሰብ ደረጃ ይህ ዓይነት ችግር የብዙዎቻችን ባሕርይ ነው (እኔም አንዱ የዚህ ባሕርይ ተሸካሚ መሆኔን እዚህ ላይ ማመን ይኖርብኛል)፡፡ ተቋማት ይህንን ግለሰባዊ ባሕርይ ወርሰው ግትር ሲሆኑ ግን ደስ አይልም፡፡ ለሚፈጠሩ ችግሮች ኃላፊነት የሚወስድ በጠፋ ቁጥር ለመፍትሄ መትጋት አይኖርም፡፡ ለመፍትሄ ካልተጋን ደግሞ መሻሻል እንደናፈቀን ይቀራል፡፡ ኃላፊነትን አለመውሰድ የአገር በሽታ እየሆነብን ይመስለኛል፤ አደገኛ ገዳይ፡፡  በጊዜ እናክመው!

Wednesday, May 20, 2015

A Tale of Two Dishes

A sub-article that I recently read on the November 2014 edition of the National Geographic Magazine took me by surprise. A study conducted by the U.S. Department of Agriculture indicated that 21% of food at the consumer level went uneaten in 2010. In other words, this food is dumped to the garbage can. The number may seem less, but here is another set of comparisons: A year’s food loss accounts for a loss of 2.5% of U.S. energy consumption, over 25% of all fresh water used for agriculture in the U.S., 300 million barrels of oil, and $115 billion.  That’s HUGE!
The USDA defines food loss as the “loss of edible food, postharvest, that is available for human consumption but is not consumed.” This definition might work better for those nations that are capable of producing food that is way more enough to feed their population, and even provide the entire world with the much-needed food supply. Having enough food on your plate, and leaving the rest for the dumping can, that’s kind of awry!
This is the case of the developed world. On the other side of the coin, the scenario is quite the opposite for the “developing” one. In this part of the world, dumping food is a luxury people cannot afford. Places where food is at scarce (especially those which became war zones or drought-prone), are battlefields where people became monsters to put their hands of what appears to be a “pearl in the desert.” Even for those who can afford to put bread on their tables, the primal issue is having something to eat, not ‘how much.’
Ironically, the “developing” world is a place that covers a large sum of cultivated land, home to various edible substances, and where the majority of the population is employed in the agricultural sector. However, it is also a playground for hunger, malnutrition, drought and famine. Of course, an ensemble of reasons can be associated with these problems. But the thing is, the world is unfair when it comes to wealth distribution.
Why do people waste food? Is it because they don’t know their limits while buying their groceries? Or is it just habitual for them to stack their refrigerators with plenty of food stuffs? I don’t get what the people of the west, who are highly private, with families shrunk in size, think when they go to the supermarkets. The food stocks a single family purchases for a week could feed around five to ten families here in Ethiopia.
Don’t get me wrong here. I’m not trying to compare the level of access to food between the two worlds. I understand there are a number of reasons associated with this phenomenon, and it’s a whole different issue not to be addressed by a “passer-by blogger” like myself. The reason that I’m commenting on this issue is the shocking disparity that our world is currently hosting is something of a ringer for contemplation.

The tale of the two dishes is an issue that calls for a wide range of discussions, and I may get back to it in the future. As a last word, though, I would like to point out one factor that, in my opinion, contributes to this unfair distribution of food throughout the world- politics. Ideological differences between nations have deprived the transfer of extra food to the less fortunate parts of the earth. When the worst famine in Ethiopian history took its stall in 1985, the UK has produced a huge surplus of wheat that was believed to feed the entire population of the East African nation, but its government has decided to dump that extra wheat to the sea. Prime Minister Margaret Thacther was asked on why her administration came to that decision, and she answered that it was because the UK “doesn’t want to hand over any assistance to a country under the leadership of a communist government.” What angers me upon reading such stories is that these people are the same ones that categorize Africans “uncivilized,” since they are the ones who failed to distinguish politics from humanity. Let’s hope such cruel and misguided perceptions would not prevail ever again.