ልጆች እና ቴሌቪዥንን አስመልክቶ ብዙ ስለማይነገርለት የወላጆች ኃላፊነት ሐሳቦችን መሰንዘር ጀምሬ ነበር፡፡ የአገራችን
ወላጆች (ሁሉም ባይሆኑ አብዛኛው) በቴሌቪዥን የሚተላለፉ ፕሮግራሞች በልጆቻቸው ባሕሪና አስተሳሰብ ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ተጽዕኖ
ጊዜ ወስደው ለማሰብ የሚጨነቁ አይመስለኝም፡፡ በቅርበት ከማውቃቸው ወላጆች መካከል በጣት የሚቆጠሩት ብቻ ናቸው የልጆቻቸውን የቴሌቪዥን
ዕይታ የሚከታተሉና ጥንቃቄ የሚያደርጉት፡፡ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ ግድ ከማጣት በተጨማሪ አለማወቅም ነው ባይ ነኝ፡፡ ስለዚህ በዚህ
ጽሑፌ ቴሌቪዥን በልጆች ላይ ስለሚያስከትለው ተጽዕኖ አንዳንድ ነጥቦችን ለማንሳት እሞክራለሁ፡፡
የሃያኛው መቶ ክፍለ-ዘመን የቴክኖሎጂ አብዮት ካፈራቸው ግኝቶች መካከል አንዱ የሆነው ቴሌቪዥን የዕድሜ ታላቁ የሆነው
ሬዲዮ ለሰው ልጅ ከሰጠው መረጃን በድምጽ የማስተላለፍ ዕድል አንድ ደረጃ ከፍ ብሎ ምስልን በማከል በአካል ልንገኝባቸው በማንችላቸው
ሥፍራዎች ሁሉ እንድንገኝ አስችሎናል፡፡ የመረጃ፣ የመማሪያና የመዝናኛ ምንጭ በመሆን የሚሰጠው ጠቀሜታ ከዘመን ዘመን እያደገና እየሰፋ
በመሄድ ላይ ነው፡፡ በተለይ በአሁኑ ዘመን ከቴክኖሎጂው መዘመን ጋር ተያይዞ በእጃችን መዳፍ ላይ እስከመገኘት ድረስ ተራቋል፡፡
በዚህ ዘመን የቴሌቪዥን ቻናሎች በጣም በዝተዋል፡፡
ብዛታቸው የፈጠረው ውድድር ቀደም ባለው ጊዜ ለተወሰኑ ሰዓታት ብቻ የነበረው የአየር ላይ ቆይታቸው ወደ ሃያ አራት ሰዓታት እንዲያድግ
አድርጓል፡፡ ድሮ በባለዘንግ አንቴና በየቤታችን ይደርስ የነበረው የቴሌቪዥን ስርጭት ዛሬ በዲጂታል ስርጭት መቀበያ ሳህን
(dish) እና የስርጭት መቀበያ መሣሪያ (decoder) እየመጣ ፣ ከሁለትና ሦስት ቻናሎች በላይ የማይታዩበት ጊዜ ቀርቶ በሺ
የሚቆጠሩ ቻናሎችን በቴሌቪዥናችን መስኮት እየተመለከትን ነው፡፡
ይህ የቻናሎችና የፕሮግራሞቻቸው መብዛት አማራጭ በመስጠት በኩል ጥሩ የሚባል ጥቅም ይኖረዋል፡፡ ተመልካቾች እንደምርጫና
ፍላጎታቸው የተለያዩ ቻናሎችን እያማረጡ መመልከት መቻላቸው መረጃ በማግኘት፣ በመማር፣ እና በመዝናናት ረገድ እርካታቸው ጨምሯል፡፡
በሌላ በኩል ግን በጊዜ ያልተገደበ እና ምርጫ-አልባ የሆነ ቴልቪዥን የመመልከት ልምድ ቀላል ያልሆነ ጉዳት ያስከትላል፡፡ ለረጅም
ሰዓታት ቴሌቪዥን መመልከት የጤናና የሥነ-ልቡና ጉዳት እንደሚያስከትል በጥናት ተረጋግጧል፡፡ ይህ ጉዳት የቅርብ ክትትል በሚያስፈልጋቸው
ሕፃናት ላይ ብቻ ሳይሆን በአዋቂዎችም ላይ የሚደርስ እንደሆነም ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ ሌላው የቴሌቪዥን ጉዳት የሚቀርቡት ፕሮግራሞች
በተመልካቾችን አስተሳሰብና አመለካከት ላይ ሊያስከትሉ የሚችሉት አሉታዊ ተጽዕኖ ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጸው የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች
በማስተማር፣ በማሳወቅ፣ መረጃ በመስጠት እና በማዝናናት ጠቀሜታቸው ከፍ ያለ ቢሆንም፣ በተለይ ደግና ክፉውን ለይቶ ለማወቅ ገና
የሆኑት ሕጻናትና ታዳጊዎች ሊመለከቷቸው የሚገቡትን ፕሮግራሞች መርጦ እንዲመለከቱ ማድረግ ካልተቻለ በወደፊት ባሕሪያቸው ላይ አደገኛ
የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ ያሳድራሉ፡፡
ጥናቶች ምን ይላሉ?
ለመሆኑ ቴሌቪዥን በሕጻናት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳድራል? ይህንን ጥያቄ ለመመለስ የተለያዩ ጥናቶች ተደርገዋል፡፡
እንደሚታወቀው በአገራችን እንኳን ይህንን ስለመሰለው ጉዳይ ቀርቶ በጣም አንገብጋቢ ስለሆኑ ጉዳዮቻችን ጥልቅ ጥናቶች አይደረጉም፣
ቢደረጉም እንኳን በተሟላ ሁኔታ ተደራጅተው ስለማይቀመጡ አግኝቶ መጠቀሙም አስቸጋሪ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ ጽሑፍ የምንመለከታቸው
ጥናቶች ባደጉት አገሮች የተደረጉትን ይሆናል፡፡ የእነዚህ ጥናቶች ውጤት በተወሰነ መልኩ ከአገራችን ሁኔታ የሚለይባቸው መልኮች ቢኖሩትም፣
መነሻው ግን ተመሳሳይ ስለሆነ ከጥናቶቹ በመነሳት ለእኛ የሚሆነውን ድምዳሜ መውሰድ እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡
ቴሌቪዥን በሕጻናት እና ታዳጊዎች ላይ የሚያሳድረውን ተጽዕኖ አስመልክቶ የሚደረጉ ጥናቶች የትኩረት አቅጣጫዎቻቸው
የተለያዩ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ፡-
1.
ልጆች በቀን ለምን
የህል ሰዓታት ቴሌቪዥን ይመለከታሉ? እና
2.
በጨቅላነት ዕድሜ ቴሌቪዥን መመልከታቸው ምን ዓይነት ውጤት ያስከትላል? የሚሉትን
ጥያቄዎች ለመመለስ ይሞከራል፡፡
ሲንዲ ስሚዝ የተባሉ የንግግር ነክ ሕመሞች ተመራማሪ (speech pathologist) “Television
Watching: Practical Advice for Parents of Young Children” በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሑፍ ወላጆች
ለምን ልጆቻቸው ቴሌቪዥን እንዲመለከቱ እንደሚያደርጉ ከልምዳቸው ተነስተው ሲያብራሩ ”አንዳንዶቹ ‘ልጄ የቴሌቪዥን ፕሮግራሙን ስለሚወደው፣’
ወይም ‘ ፊደላትን ስለሚማርበት’፣ ሌሎቹ ደግሞ ‘ልጄ ምግብ አማርጣ የምትመገብ ናት፤ ቴሌቪዥኑ ከተከፈተ ግን እየበላች እንደሆነ
ስለማታስተውለው ያለምርጫ ትመገባለች፣’ ወይም ‘እኔ እራት ሳዘጋጅ ልጄ ቴሌቪዥን በማየት ስለምትጠመድ አትረብሸኝም’ የሚሉና መሰል
ምክንያቶችን ይሰጣሉ” ይላሉ፡፡
ባለሙያዋ በጥናታቸው ቴሌቪዥን ዕድሜያቸው ከ2 እስከ 11 ዓመት ድረስ በሆኑ ሕጻናትና ታዳጊዎች ላይ የሚያስከትለውን
ተጽዕኖ ተመልክተዋል፡፡ የጥናታቸው ትኩረት ሕጻናትና ታዳጊዎች በቀን ውስጥ ለስንት ሰዓታት ቴሌቪዥን እንደሚመለከቱ የሚፈትሽ ሲሆን፣
በተገኘው ውጤት መሠረት በዩናይትድ ስቴትስ አንድ ልጅ በአማካይ በቀን ከ4 ሰዓታት በላይ ቴሌቪዥን የሚመለከት ሲሆን፣ በካናዳ እና
አውስትራሊያ በቀን ከ2 ሰዓታት በላይ፣ እንዲሁም በዩናይትድ ኪንግደም ከ2 ሰዓት ተኩል በላይ ልጆች ቴሌቪዥን ይመለከታሉ፡፡ ከዚህ
በመነሳት ”አንድ ልጅ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲያጠናቅቅ በክፍል ውስጥ ካሳለፈው ጊዜ ይልቅ በቴሌቪዥን ፊት ተቀምጦ ያሳለፈው
ጊዜ ይበልጣል” ይላል ጥናቱ፡፡
ይህ የልጆች የቴሌቪዥን ልምድ ታዲያ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ባይ ናቸው ሲንዲ ስሚዝ፡፡ ጉዳቶቹ በሦስት ዋና ዋና
ክፍሎች ተመድበዋል፡፡
1.
አካላዊ ጤና፡- በምዕራባዊያን አገሮች
ለሕጻናት ውፍረት በዋነኛነት ምክንያት ተደርገው ከሚወሰዱት ነገሮች መካከል አንዱ ልጆች ቴሌቪዥን፣ ቪዲዮና ዲቪዲ ለመመልከት፣ እንዲሁም
የኮምፒዩተር ጌም ለመጫወት ሲሉ በርካታ ሰዓታትን ተቀምጠው ማሳለፋቸው ነው (ይህ ልምድ ወደ አገራችንም በአሁኑ ጊዜ እየመጣ መሆኑን
ልብ ይሏል)፡፡ በዚህም የተነሳ የልጆች የአካል እንቅስቃሴ ልምድ ቀላል በማይባል ደረጃ እየቀነሰ ይገኛል፡፡
2.
ሥነ-ባሕሪያዊ ጤና፡- እንደ ባለሙያዋ ገለጻ፣
አንዳንድ ለሕጻናት ተብለው የሚዘጋጁ ፕሮግራሞች በአማካይ በሰዓት 20 የሚደርሱ የግጭት/ረብሻ ትዕይንቶችን የያዙ ናቸው፡፡ እነዚህ
ትዕይንቶች በካርቱን ፊልሞች ላይ ከሚታየው የገጸ-ባሕርያት የእርስ በርስ መጋጨት አንስቶ በእውነተኛ ገጸ-ባሕርያት ከሚተወኑ የረብሻ
(violence) ድርጊቶች ድረስ ይዘልቃሉ፡፡ አንዳንድ ባለሙያዎች ለረዥም ጊዜ የሚዘልቅ የሕጻናትና ታዳጊዎች የቴሌቪዥን ዕይታ
ድርጊቶችን መሞከር፣ ፍርሃትን፣ እና ችግሮችን በኃይልና በጉልበት የመፍታት ዝንባሌን ያዳብራሉ ሲሉ ይከራከራሉ፡፡
3.
ቋንቋ እና አጠቃላይ
ትምህርት፡- ይህንን ክፍል አስመልክቶ በርካታ ጥናቶች የተደረጉ ሲሆን፣ ውጤታቸው የተለያዩ ቢሆንም በአጠቃላይ ግን ”ዜናው ጥሩ
አይደለም” ይላል የስሚዝ ጽሑፍ፡፡ እንደነዚህ ጥናቶች ከሆነ ለማስተማሪያ ተብለው የሚዘጋጁት ፕሮግራሞች ሳይቀሩ በጨቅላ ሕጻናት
የቋንቋ ትምህርት ብቃት ላይ መቀነስን አስከትለዋል፡፡
(ይቀጥላል)