Monday, October 15, 2018

እጅግ አስፈላጊው ሰው!



አብዱ አሊ ሂጂራ፤ ይህ ሰው በቀደመው ጊዜ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ይቀርብ በነበረው “እርስዎም ይሞክሩት” የጥያቄና መልስ ፕሮግራም ላይ ሕግ-ነክ ለሆኑ ጥያቄዎች ሙያዊ ማብራሪያ በመስጠት የሚታወቅ፣ በዳኝነት እና በሬጅስትራርነት ለበርካታ ዓመታት አገሩን ያገለገለ አንጋፋ የሕግ ባለሙያ ነው፡፡ በሬዲዮ ያዳበረውን የሚዲያ ልምድ ይዞ በሪፖርተር የአማርኛ ጋዜጣ በዋና አዘጋጅነት ሠርቷል፡፡ ከዚያ በኋላም በሸገር ኤፍ ኤም “ረ በሕግ” የተባለውን ፕሮግራም አዘጋጅቶ በማቅረብ ሕግን ለማንኛውም ዜጋ በሚገባ መንገድ አስተምሯል፡፡ አሁን ደግሞ ከበሳሏ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ ጋር በመሆን በ”ሸገር ካፌ” ፕሮግራም ላይ ወቅታዊ የአገራችንና ዓለም አቀፍ ጉዳዮችን በሕግ ዓይን በመተንተን ድንቅ ሥራ እየሠራ ይገኛል፡፡
ከለውጡ ወዲህ የአገራችንን ወቅታዊ ዜናና መረጃ መከታተል የጀመሩ አንዳንድ ሰዎች አብዱ በጠንካራ አገላለጽ የሚያነሳቸውን የሕግ ሕጸጾች ሲተች ሲሰሙ “እስከዛሬ የት ቆይቶ ነው ዛሬ የሚያወራው?” ይላሉ፡፡ ሰውየው ግን፣ አቶ መለስ ዜናዊ ጠቅላይ ሚኒስትር በነበሩበት ጊዜ ሳይቀር ከፓርላማው የሕግ አወጣጥ ሥርዓት አንስቶ እስከ ካቢኔው የመመሪያዎች መጣረስ ድረስ ሕግና ታሪክን እያጣቀሰ የሞገተ የሙያው ሰው መሆኑ የማይካድ እውነታ ነው፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ እስከ ፍትሐ-ነገሥት፣ ከ1948ቱ ሕገ-መንግሥት እስከ 1987ቱ እና የተለያዩ ሕጎች፣ አዋጆችና ደንቦች፣… ድረስ፣ አብጠርጥሮ በመመርመር መንግሥትንና ሕዝብን  ሲመክር የኖረ ደፋር ባለሙያ እንደሆነ የምናውቀው ሁሉ እንመሠክራለን፡፡ የዶ/ር ዐቢይን አስተዳደር መልካም ጎኖች በማወደስ ብቻ ሳይወሰን ስህተቶቹንም ጭምር ሕግና ሕግን ብቻ ተከትሎ እየነቀሰ ማስተካከያ እንዲያደርግ መክሯል (በነገራችን ላይ፣ መዓዛም ብትሆን “ዶ/ር ዐቢይ አሞግሰውኛል፣ የቦርድ አባል አድርገውኛል” በሚል ሳትደለል ስህተቶችን በመንቀስና በመጠቆም የምታደርገው ተግባር ሊደነቅ ይገባዋል)፡፡
ዶ/ር ዐቢይ ሊጠቀሙባቸው ከሚገቡ ሰዎች መካከል አብዱ አሊ ሂጂራ አንደኛው ነው!



No comments:

Post a Comment