ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በብዛት ከምንሰማቸው ጉዳዮች መካከል ”ፊልም፣ ቴሌቪዥን፣
እና ሕጻናት” አንደኛው ነው፡፡ የዚህ ጉዳይ ዋነኛ መነሻ በቴሌቪዥን የሚተላለፉ ፕሮግራሞች እና ፊልሞች በሕጻናት እና ታዳጊዎች ላይ አሉታዊ
ተጽዕኖ ማሳደራቸው ይመስለኛል፡፡ ወቅቱ ክረምት ነውና ሕጻናት እና ታዳጊዎች ከእነዚህ ፊልሞች እና ፕሮግራሞች ጋር ሰፋ ያለ ጊዜ
ማሳለፋቸው (በአብዛኛው ካለወላጅ እና አሳዳጊ ክትትል) አሳሳቢነቱ አያጠያይቅም፡፡
መወያየቱ፣ መመካከሩ፣ እና መፍትሄ መፈለጉ የሚደገፍ ነው፤ ሆኖም የውይይቱና የክርክሩ ተሳታፊዎች ብዙውን ጊዜ ሲያነሱት
የማልሰማው አንድ ጉዳይ ቢኖር የወላጅ/አሳዳጊ ኃላፊነት ነው፡፡ ወላጆችና አሳዳጊዎች ልጆቻቸው ስለሚመለከቷቸው የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችና
ፊልሞች ምን ያህል ያውቃሉ? የሚመለከቱትን ፕሮግራም እንዴት መቆጣጠር
ይችላሉ? እነዚህንና መሰል ጥያቄዎችን አንስቶ የሚወያይና የሚያወያይ፣ የሚያጠናና የሚመራመር አካል (ባለሙያ ወይም ተቋም) እስካሁን
ድረስ አላጋጠመኝም፡፡ በአብዛኛው ተወቃሽ ተደርገው የሚነሱት የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ናቸው፡፡ ስለወላጆችና አሳዳጊዎች ድርሻ ግን ምንም
ነገር ሲነገር አልሰማሁም፣ የተጻፈም ነገር እስካሁን ድረስ አላገኘሁም፡፡
ስለዚህ ጉዳይ ማሰብ ከጀመርኩ ከአሥር ዓመታት በላይ አልፏል፣ ይህ ጽሑፍ ከተጀመረ ደግሞ ሁለት ዓመት ሊሆን ነው፡፡
ነገር ግን ርዕሰ-ጉዳዩ ሰፊ ከመሆኑ አንጻር ጊዜ ወስዶ ማሰብ ስላስፈለገኝና መጠነኛ ስንፍናም ተጨምሮበት ጽሑፉ እስካሁን ድረስ
ከአንድ አንቀጽ በላይ ሳይሄድ ቆይቷል፡፡ አሁን ላይ እንደአዲስ ይህንን ጉዳይ እንድመለስበት ያደረገኝ በልጆች አስተዳደግ ላይ በቅርባችን
የማያቸው ነገሮች የተለያዩ ጥያቄዎችን የሚያስነሱ ሆነው ስላገኘኋቸው ነው፡፡
ከላይ እንደጠቀስኩት ”ቴሌቪዥን፣ ልጆች፣ እና የወላጅ ኃላፊነት” ስለሚለው ጉዳይ ማሰብ ከጀመርኩ ቆይቷል (በትክክል
ከአሥራ ሁለት ዓመታት በፊት ነው)፡፡ የዛሬ አሥራ አምስት ዓመት ገደማ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አማካይነት በአገር ውስጥ ይተላለፍ
የነበረውን ”ቲቪ አፍሪካ” የተባለ ቻናል ታስታውሱታላችሁ፡፡ በወቅቱ ይህ ቻናል ለብዙ ተመልካቾች የመረጃና የመዝናኛ አማራጭ ሆኖ
በመቅረቡ ተወዳጅነትን ለማትረፍ ጊዜ አልፈጀበትም፡፡ የተወዳጅነቱን ያህል ብዙ ትችቶችንም አስተናግዷል፡፡ ቁጥራቸው ቀላል የማይባል
ሰዎች ”ቲቪ አፍሪካ ልጆቻችንን እያበላሸ ነው” በማለት በተደጋጋሚ ሲወቅሱት ይሰማ ነበር- በጊዜው፡፡
ከእነዚህ ትችቶች መካከል ይበልጥ ትኩረቴን የሳበውንና ስለወላጅ ኃላፊነት እንዳስብ ያደረገኝን ሐሳብ የሰማሁት በ1995
ዓ.ም. ነበር፡፡ በወቅቱ በአንድ ስብሰባ ላይ አንድ ዕውቅ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የትውልዱን ሥነ-ምግባር አስመልክተው
ሲናገሩ ”አኔ እኮ ዛሬ ልጆቼን አላሳድግም፣ ልጆቼን የሚያሳድግልኝ
ቲቪ አፍሪካ ነው” ብለው ነበር፡፡ ይህ አባባል የስብሰባውን ተሳታፊዎች ፈገግ አሰኝቶ ነበር፣ እኔንም አስቆኛል፣ ከሳቁ በኋላ ግን
ቀደም ብሎ ከሰማኋቸው ትችቶችና ወቀሳዎች ጋር ተዳምሮ ነገሩ ከነከነኝ፡፡ ”የቴሌቪዥናቸውን አንቴናና የቲቪ አፍሪካን ፍሪኩዌንሲ
አስተካክለው ቤታቸው ያስገቡት እራሳቸው ወላጆች ሆነው ሳለ ቻናሉን ለምን ይተቻሉ? ስለሚተላለፉት ፕሮግራሞች የሚሰጠውን ማሳሰቢያስ
ለምን አይከታተሉም?” ብዬም ጠየቅሁ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የቲቪ አፍሪካ ፕሮግራሞች ይዘትና የስርጭት መርሐ-ግብር ምን እንደሚመስል
ማወቅ ስለፈለግሁ የቲቪ አፍሪካን ድረ-ገጽ ጎበኘሁ፡፡
በኢቲቪ-2 የሚተላለፈው የቲቪ አፍሪካ ስርጭት ከቀኑ 11 ሰዓት እስከ እኩለ-ሌሊት ድረስ የሚዘልቅ ቢሆንም፣ ቲቪ
አፍሪካ ግን ለ24 ሰዓታት የተለያዩ ፕሮግራሞችን (ዜና፣ ድራማ፣ ሶፕ ኦፔራ፣ ፊልም፣ ሙዚቃ፣…) የሚያቀርብ ነጻ ቻናል መሆኑን
ከድረ-ገጹ ላይ ለመረዳት ቻልኩ፡፡ በድረ-ገጹ ላይ የተቀመጠው የፕሮግራሞች ዝርዝር የእያንዳንዱን ፕሮግራም ዓይነትና ይዘት፣ እንዲሁም
የተመልካቾች የዕድሜ ገደብ የሚገልጽ አጭር መግለጫ የያዘ ነው፡፡ በነገራችን ላይ የፕሮግራሞች የዕድሜ ገደብ መግለጫ በተለይ ፊልሞችና
ድራማዎች በቴሌቪዥን መቅረብ ከመጀመራቸው በፊት በግልጽ ቋንቋ ለተመልካቾች ይገለጽ ነበር፡፡
ከዚህ
በኋላ ነው እንግዲህ የወላጆችን ኃላፊነት አስመልክቶ ማሰብ የጀመርኩት፡፡ የቴሌቪዥን ቻናሉ ”የማስተላልፈው ፕሮግራም ከዚህ ዕድሜ
በላይ ላሉ ተመልካቾች የሚሆን ነው” ብሎ ካሳወቀ፣ ቀሪው ኃላፊነት የወላጅ፣ የቤተሰብ፣ የአሳዳጊ ወይም የሞግዚት ነው፡፡ ይህንን
ማድረግ የማይችሉ ወላጅና ቤተሰቦች፣ ቻናሉን ጥፋተኛ አድርገው ለመውቀስ የሚያስችላቸው ምንም ዓይነት ምክንያት አለ ብዬ አላምንም፡፡
ሥራቸውን አልሰሩማ! (ይቀጥላል)