Sunday, June 20, 2021

የአንድ ዜጋ መልዕክት- በምርጫ ዋዜማ

ይህችን አጭር ጦማር ስጽፍ፣ ዕለቱ እሁድ፣ ሰኔ 13 ቀን 2013፣ ሰዓቱ ከምሽቱ 12፡30 ነው፡፡ ብዙ የተባለለትንና የተባለበትን፣ ተስፋ፣ ፍርሃት እና ስጋት የሚንጸባረቅበት እና የኢትዮጵያ መጻኢ ዕድል እንደሚወስን የሚጠበቀው አገራዊ ምርጫ ሊካሄድ 11 ሰዓት ከ30 ደቂቃ ይቀረዋል፡፡

ከሰባት ዓመታት በፊት በተካሄደው የ2007 የኢትዮጵያ ምርጫ ወቅት ብዙ አስገራሚ ሁነቶችን ታዝበን ነበር፡፡ የፈዘዘ የፓርቲዎች ቅስቀሳና ክርክር፣ በሕጸጾችና በሕገወጥ አካሄዶች የተሞላ የመራጮች ምዝገባ፣ ሕግን የተላለፈ የቤት ለቤት የምርጫ ቅስቀሳ፣ በምርጫ ቀን ሳይቀር ያልተቋረጠ የምረጡን ጥሪ፣ እና በዓለም ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የ100 ፐርሰንት አሸናፊነት፡፡

ይህ ሁሉ ሂደት ታልፎ የተመሠረተው “መንግሥት” መንፈቅ ሳይሞላው በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተነሱ ተቃውሞዎች ግራ ተጋብቶ የአገሪቱም ጉዞ ግራ የተጋባ ሆኖ ነበር፡፡ ለሁለት ዓመታት እየተንገራገጨ የሄደው ይህ ጉዞ በተለይ በ2010 ይበልጥ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ገብቶ፣ ሕዝባዊው ተቃውሞም ይበልጥ ሲቀጣጠል የሕዝቡን የለውጥ ፍላጎት የተረዱና ለውጥ እንደሚያስፈልግ የተረዱ የገዢው ፓርቲ አመራሮች ወደፊት መጥተው ተግባራዊ የለውጥ እንቅስቃሴ አደረጉ፣ በዚህም አዲስ የለውጥ አመራር የአገሪቱን የፖለቲካ አመራር ተረከበ፡፡

ከዚያ ወዲህ ባለፉት ሦስት ዓመታት ብዙ ክስተቶችን አስተናግዳለች፣ ኢትዮጵያ፡፡ ተግባራዊ የፖለቲካ ለውጥ፣ አዳዲስ አሠራሮች፣ አዲስ ተስፋ፣…፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የከፉ የብሔር ግጭቶች፣ ማንነትን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች፣ የአገር መፍረስ ስጋት፣…፡፡ ብዙዎች ወገኖቻችንን ከስደት አስመለስን፣ በደስታ አነባን፣ ፈነጠዝን፣…፡፡ ብዙዎች ወገኖቻችንን ሰምተን በማናውቀው ጭካኔ አጣን፣ በዘመናት ልፋት የተገኘ ሀብትና ንብረት ወደመብን፣…፡፡ ብዙ ወገኖቻችን በስደትና መፈናቀል ተጎዱብን፣…፡፡

ይህንን ሁሉ ተለዋዋጭ ሁኔታ ያስተናገደችው ኢትዮጵያችን ግን ዛሬም አለች፣ ትናንትን እንዳለፈች ሁሉ ዛሬንም አልፋ ነገንም ትኖራለች፡፡ ይህ የሚሆነው ግን እኛ ኢትዮጵያዊያን አገራችንን ለማኖር የአገራችን ባለቤቶች እኛ መሆናችንን ስናረጋግጥ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ዕድላችንን እንጠቀምበት!

የምርጫ ካርድ ያወጣን ኢትዮጵያዊያን በሙሉ፣ ነገ ካርዳችንን እንጠቀምበት፡፡ ኢትዮጵያን ያሻግራል፣ ወደከፍታዋ ያደርሳል፣ የዛሬውን ጨለማ ነገ ይገፍልናል ብለን የምናምነውን እንምረጥ፡፡ ውጤቱ ምንም ይሁን፣ ማንም ያሸንፍ፣ ግን ተአማኒ ምርጫ በማድረግ የአገራችንን ነገ ብሩህ ለማድረግ ድርሻችንን እንወጣ፡፡ ከተሳካልን፣ ኢትዮጵያ ላይ የሚያሟርቱትን ሁሉ አሳፍረን ለነገዋ የተሻለች ኢትዮጵያ መገንባት አሻራችንን እናሳርፋለን፡፡ የእኛ ድርሻ የሚስማማንን መርጠን መንግሥት እንዲሆንና አገራችንን እንዲያረጋጋ ዕድል መስጠት ነው፡፡ ይህንን እናድርግ!

ፈጣሪ ኢትዮጵያን እና ሕዝቧን ይባርክ!


Thursday, February 21, 2019

The Bliss of Imperfection

After watching the new movie "What Men Want"over the weekend, a question popped in my mind: "What would happen if humans were 'the almighty?'" My answer? "It would've been a disaster!"
Ali Davis, a tough-talking, no-nonsense sports agent (played by Taraji P. Henson, from the hot Fox drama "Empire"), gained the ability to listen to men's inner thoughts, after drinking the grouse-tasting  jasmine tea prepared by the odd-looking psychic, Sister (portrayed by singer/actress Erykah Badu), and a nasty concussion at her friend's bachelorette party. Though she was terrified at first of her newfound ability, Davis was convinced to use it for her advantage in winning over her male colleagues on her quest of becoming partner at the company she works for. She became successful, but the talent of thought listening gravely damaged her love life. 
How would we feel, if we are in such a position? Listening to what people think is like... becoming God! Imagine what God is doing all day and all night, listening and answering to prayers, complaints, questions, and demands of billions of His greatest creations. He can answer, and He can deliver, because He is God! This is something that we, the humans, can not handle. 
In "Bruce Almighty," another Hollywood movie, out back in 2003, we can see how humans behave, complaining of their apparent "misfortunes," and blame God for it. Bruce Nolan (Jim Carrey), an out-of-luck news reporter, who complains about God too often, met God (Morgan Freeman) and given almighty powers to run the world. He learned the hard way that being God is the toughest job there is during the course, a great lesson for us to realise that being "whole" is not good for human beings. 
I see people trying to become "perfect" in life, or the least, pretend to look perfect in the eyes of the others. We also wish to become "superhuman," who knows and can do anything. But this is not possible, and there is a reason why. God knows best, and He knows that if humans were perfect and almighty, they would turn the world upside down, knowingly or unknowingly. So the lesson I've learned in life (and after watching the film) was: Don't thrive to become perfect, for it is the recipe for disaster! What we are is enough for us to live another day, and being imperfect is often a bliss. Just try to be good and efficient; that's perfection in human standards. Leave being the almighty to the Big Boss upstairs!

Sunday, December 2, 2018

ማደግ ከፈለግን እንከባበር!


ከሁለት ወራት በፊት በቡራዩ ከተማ ተፈጥሮ በነበረው ግጭት ለተጎዱ ወገኖች ቴዲ አፍሮ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ተከትሎ በማኅበራዊው ሚዲያ ላይ የደረሰበትን ትችትና ዘለፋ አስመልክቶ የተሰማኝን ቅሬታ በፌስቡክ ገጼ ላይ አሥፍሬ ነበር፡፡ በጊዜው በጽሑፌ ላይ ከተሰጡ አስተያየቶች መካከል “ዘፋኝና ዘፈን አገር አያቀናም፣ አገር የምትበለጽገው በሳይንስና ቴክኖሎጂ ብቻ ነው” የሚል ይገኝበት ነበር፡፡ ለዚህ አስተያየት “ሳይንስና ቴክኖሎጂ ብቻ?” የሚል ጥያቄ-አዘል ምላሽ ስሰጥ፣ “አዎ፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ብቻ!” የሚል ቁርጥ ያለ መልስ ነበር የተሰጠኝ፡፡
ከአስተያየት ሰጪው ጋር በሐሳብ ለመግባባት ሞክረን ስላልቻልን ላለመስማማት ተስማምተን ነገሩ በዚሁ ቆመ፤ ከዚህ በኋላ ግን፣ አስተያየት ሰጪውን ልጠይቃቸው ይገባኝ የነበረ፣ ግን የዘነጋሁትን ጥያቄ አስታወስኩ፤ “ብቻውን አገር ያቀና ሙያ አለ?” የሚል፡፡ ምን ያደርጋል? ጊዜው ካለፈ በኋላ ሆነና ሳልጠይቃቸው በመቅረቴ ቆጨኝ፡፡ ቢሆንም፣ ይህ ርዕስ የማይሞት አጀንዳ በመሆኑ በዚህ ጽሑፍ ላይ አቋሜን ለማቅረብ ወደድኩ፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ፣ በርካታ ውብ እሴቶች ያሏት አገር ብትሆንም፣ በዚያው ልክ ደግሞ በቁጥር የበዙ ድክመቶችና ከእነዚህ ድክመቶች የሚመነጩ ችግሮችን የተሸከመች ናት፡፡ ከእነዚህ ድክመቶች መካከል አንደኛው የአስተሳሰብ ድክመት ነው፡፡ የእኛ የኢትዮጵያዊያን የአስተሳሰብ ድክመት መገለጫዎች በርካታ ናቸው፣ ለዛሬው ሐሳቤ መነሻ የሆነው የአስተሳሰብ ድክመታችን መነሻ ሙያን መሠረት ያደረገ መናናቅ ነው፡፡
በኢትዮጵያ በፊውዳላዊውም ሆነ ከዚያ በፊትም በነበሩት ሥርዓቶች ሰዎች በሙያቸው የተነሳ መናቃቸውና መገለላቸው የተለመደ ሆኖ ቆይቷል፡፡ ቆዳ ሠሪውን “ፋቂ፣” ነጋዴውን “መጫኛ ነካሽ፣   “ ልብስ ሰፊውን “ክር በጣሽ፣” ሸክላ ሠሪውን “ቡዳ፣”… እያሉ መናቅ የማኅበረሰቡ ወግና ዐቢይ መገለጫ የነበረባቸው ዘመናት ሩቅ አልነበሩም፡፡ በዚህም ምክንያት እነዚህ የማኅበረሰቡ ክፍሎች ጋብቻ እስከመከልከል፣ በአገር መቀመጫ እስከማጣትና አልፎ ተርፎም እስከመገደል ድረስ መከራ ተቀብለዋል፡፡
ይህንን አግላይ አስተሳሰብ ለመቀየር ተራማጅ አስተሳሰብ የነበራቸው የአገራችን መሪዎች በየሥልጣን ዘመናቸው ሙከራ ማድረጋቸው አልቀረም፡፡ እንደ ምሳሌም፣ ዳግማዊ አጼ ምኒልክ ጥር 17 ቀን 1900 ዓ.ም. ባስነገሩት አዋጅ “ሠራተኛን በሥራው የምትሰድብ ተወኝ” የሚል ጠንካራ ኃይለ-ቃል መናገራቸውን መውሰድ ይቻላል፡፡
ዘመናት አልፈው፣ “ኋላ-ቀር እና ጎታች” የተባለው ሥርዓት “አብዮታዊና ተራማጅ” በተባለው ሥርዓት ሲቀየር፣ ሙያን መሠረት ያደረገ የንቀትና የማግለል አስተሳሰብን ለመቀየር የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል፤ በዚህም አንፃራዊ ለውጥ ታይቷል፡፡ ይሁንና በመንግሥት ደረጃ የተወሰዱ እርምጃዎች ተቋማዊውን አግላይነት ቢቀንሱም፣ ማኅበረሰባዊውን አግላይነት ሙሉ በሙሉ አጥፍተዋል ማለት አያስደፍርም፡፡ “ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን መከተል ጀምረናል” በተባለበት በአሁኑ ጊዜ፣ ከቀደመው ጊዜ የተሻለ ነገር ቢታይም፣ አሁንም ማኅበረሰባዊው አመለካከት ሙሉ በሙሉ አልተቀየረም፡፡ በተለይ በኪነ-ጥበቡ ዘርፍ ላይ ይህ በጣም ጎልቶ ይታያል፡፡
በመግቢያዬ ላይ ያነሳሁት የራሴ ገጠመኝ ምናልባት ቀላሉ ማሳያ ነው፣ ከዚህ የባሱ አግላይ አስተያየቶችን ባለፉት ዓመታት ሰምቻለሁ፣ አንብቤያለሁ፡፡ አልፎ ተርፎም፣ ሃይማኖታዊ ልብስ የተላበሱ ማግለያዎችንም በብዛት ተመልክቻለሁ፡፡ ወደእነዚህ አስተያየቶችና ወደክርክሩ በዚህ ጽሑፍ ለመግባት አልፈልግም፤ ራሱን የቻለ ትልቅ ርዕስ ስለሆነ፡፡ በእነዚህ ሐሳቦች መነሻነት ግን፣ “ሙያን ማበላለጥ አገር አያቀናም፣ አያበለጽግም” የሚለውን ሐሳቤን ለማካፈል ነው ዓላማዬ፡፡
በዓለም ላይ፣ በየትኛውም አገር፣ አንድ ሙያ ብቻውን አገር አቅንቶና ገንብቶ አያውቅም፤ የግድ የሌላ ሙያ ድጋፍና ትብብር ያስፈልገዋል፡፡ የፌስቡኩን አስተያየት ብንወስድ፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተሠማሩ ባለሙያዎች ሥራቸውን በንቃት ለማከናወን ሙዚቃን ይጠቀማሉ፡፡ ለምሳሌ፣ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና የኮምፒውተር ሳይንስ ባለሙያዎች፣ ባለብዙ መስመር የፕሮግራም ኮዶችን ለመፃፍ ረዥም ጊዜ ያስፈልጋቸዋል፣ ሥራው የሐሳብ (concept) ሥራ ስለሆነ አዕምሮ በእጅጉ ይወጠራል፡፡ ይህንን የአዕምሮ ውጥረት ለማቃለል ባለሙያዎቹ በሥራቸው ላይ ሆነው ሙዚቃ በጆሮ ማዳመጫ እያዳመጡ የሚሠሩበት ጊዜና ሁኔታ ብዙ ነው፡፡ በዋና ዋናዎቹ የዓለማችን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የሚሠሩ ባለሙያዎችን በሥራ ቦታቸው ላይ ሆነው ስናያቸው ይህንን በሚገባ እንመለከታለን፡፡ ሙዚቃው የባለሙያዎቹን አዕምሮ ባያረጋጋው ዛሬ የምንደነቅባቸውን የቴክኖሎጂ ውጤቶች ማግኘት ቀላል ሊሆንልን እንደማይችል መገመት ይቻላል፡፡ ይህ የቴክኖሎጂና የሙዚቃ ቁርኝት ምሳሌ “ዘፋኝና ዘፈን አገር አያቀናም” የሚለውን ክርክር ውድቅ የሚያደርግ አንድ ምሳሌ ይመስለኛል፡፡
የሙያዎች የእርስ በርስ መደጋገፍ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ ነው፡፡ እያንዳንዳችን የተሰጠን የየራሳችን ስጦታና መክሊት አለን፡፡ ፈጣሪ ለሁላችንም መክሊታችንን ሲሰጠን ምክንያት አለው፤ ምክንያቱ ሁላችንም በራሳችን ሙሉ እና ፍጹም አለመሆናችን ይመስለኛል፡፡ ስለሆነም፣ የአንዳችን ችሎታና ሙያ ለሌላችን አስፈላጊ ነው፡፡
ሁሉ አናጢ፣ ሁሉ ግንበኛ፣ ሁሉ ጠራቢ፣ ሁሉ ለሳኝ፣… ቢሆን ቤት አይገነባም፡፡ ሁሉ ሐኪም፣ ሁሉ ነርስ፣ ሁሉ መርፌ ወጊ፣… ቢሆን ሕመምተኛ አይድንም፡፡ ሁሉ መሐንዲስ፣ ሁሉ ወታደር፣ ሁሉ መምህር፣… ቢሆንም አገር አትቀናም፣ አትበለጽግም፡፡ የእያንዳንዳችን ዕውቀት፣ ችሎታ እና ተሰጥኦ ድምር ውጤት ናት አገራችን፡፡ አንዳችን በምንሠራው ላይ ሌላችን የራሳችንን ጡብ እያስቀመጥን ነው “ኢትዮጵያ” የምትባለውን ታላቅ አገር የገነባነው፣ የምንገነባውም፡፡
ታዲያ ለምንድን ነው የአንዳችንን ሙያ ሌላችን መናቃችን? ብቻችንን ለማንኖርባት ምድር ተከባብሮ መኖር እንደምን ተሳነን? ሙሉ ሳንሆን ሌላ ሰው እና ሌላ ሙያ እንደሚያስፈልገን ለምን መረዳት አቃተን?
ልብስ ሰፊው ልብሳችንን ካልሰፋ ዕርቃናችንን ወደሥራችን መሄድ እንደማንችል፣ ጫማ ሠሪው ጫማ ባይሠራልን በባዶ እግራችን ወደየትም መንቀሳቀስ እንደሚሳነን ለምን እንረሳለን? እነዚህን ሰዎች ንቀን የት ልንደርስ ይሆን?
ተናንቀን አገር አንገነባም፤ እንኳን ተናንቀን፣ “ተከባብረን ኖረናል” ባልንባቸው ዘመናት እንኳን ኢትዮጵያ ከድህነት አልወጣችም፡፡ ዛሬ “አድገዋል” የሚባሉትና እኛም በባሌም፣ በቦሌም ልንገባባቸው መከራ የምናይባቸው አገራት የበለጸጉት ለእያንዳንዱ ሙያ ተገቢውን ክብር እና ዕውቅና ስለሰጡ ነው፣ መስጠት ብቻም ሳይሆን፣ የእያንዳንዱ ሙያ መደጋገፍ ለልማት አስፈላጊ እንደሆነ ተረድተው ነው፡፡ ስለዚህ፣ ማደግ ከፈለግን እንከባበር!
(በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ኅዳር 22/2011 ዕትም ላይ የወጣ)

Wednesday, November 28, 2018

ለሚዲያ ሰዎቻችን አንዳንድ ማረሚያ፡-


ከዓመታት በፊት የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ (ዶይቸ ቬለ) የአማርኛ አገልግሎት ጋዜጠኛ የነበረው አቶ ጌታቸው ደስታ፣ በአንድ ቃለ-መጠይቅ ላይ ስለዜና አሠራራቸው ተጠይቆ ሲመልስ፣ “የዓለም ዜናዎችን ስንሠራ የተለያዩ አገራት ሰዎችን ስም መጥቀስ ስላለብን፣ በስም አጠራር ላይ ስህተት ላለመሥራት በጣም እንጠነቀቃለን፤ ለምሳሌ የቻይና ስም በዜናችን ላይ ካለ፣ የእኛ ቢሮ ካለበት ፎቅ በላይ ወዳለው የማንዳሪን ቋንቋ አገልግሎት ቢሮ ሄደን ስሙን እስከነአጠራሩ ጠይቀን መጥተን ተለማምደን ነው የምናነበው፡፡ እነሱም የኢትዮጵያ ሰው ስም በዜናቸው ውስጥ ካለ ወርደው መጥተው፣ ጠይቀውና አጥንተው ያነባሉ፡፡” ብሎ ነበር፡፡ 
አብዛኛዎቹ የአገራችን ጋዜጠኞች (ሁሉም ማለት ያስደፍራል)፣ በሚሠሯቸው ዜናዎችና ፕሮግራሞች የሚጠቀሟቸውን ቃላት፣ ስያሜዎች እና ስሞችን በትክክለኛው መንገድ ለመጥራት ሲቸገሩ አያለሁ፣ እሰማለሁ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ፣ የተለያዩ አገልግሎቶችና ተቋማትን ስምም በአግባቡ ሳይጠሩ ሲቀሩ ያጋጥመኛል፡፡ ችግሩ ለሥራው ትኩረት ሰጥቶ በደንብ አለመዘጋጀት ነው፡፡ እናም ለዚህ ትኩረት ቢሰጡ፣ በተለይ በዚህ የኢንተርኔት ዘመን፣ ብዙ የመማሪያ አማራጮች ስላሉ፣ እነርሱን ቢጠቀሙ ተገቢ ነው እላለሁ፡፡
ለአሁኑ ግን፣ አንድ ሁለት ነጥቦችን እንዲያስተካክሉ ለመጠቆም እፈልጋለሁ፡፡
·         በአንድ ወቅት፣ ስለአንድ የዘረፋ ወንጀል የሚዘግብ ዜና በሬዲዮ ሲነበብ ሰምቼ ነበር፡፡ በዜናው ውስጥ፣ የዝርፊያውን ፈጻሚዎች ለመለየት በደህንነት ካሜራ (CCTV) የተቀረጸውን ምስል ፖሊሶች እየመረመሩ እንደሆነ የሚገልጽ ዓረፍተ-ነገር ነበረበት፡፡ ታዲያ፣ ጋዜጠኛው “CCTV” የሚለውን ምህፃረ-ቃል የተረጎመመበት መንገድ አስቂኝ ነበር፣ እሱ የተረጎመው “የቻይና ማዕከላዊ ቴሌቪዥን (China Central TeleVision) በሚለው የቻይና ብሔራዊ ቴሌቪዥን ስም ነው፡፡ በዜናው ዐውድ ውስጥ ግን “CCTV” ማለት “Closed Circuit TeleVision” ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጋዜጠኞች፣ ምህፃረ-ቃል ሲገጥማችሁ በደንብ አጣርታችሁ ፍቱ፣ አለበለዚያ ባትተነትኑት ይመረጣል፡፡
·         ብዙ ጊዜ ከኢንተርኔት ገጾች የሚገኙ መረጃዎችን ስትጠቅሱ “እገሌ የተባለው ድረ-ገጽ” ትላላችሁ፡፡ “ድረ-ገጽ” የእንግሊዝኛውን “website” ለመተካት ጥቅም ላይ የዋለ ቃል ነው፣ ትርጉሙ ግን ትክክል አይደለም፡፡ “ድረ ገጽ” በእንግሊዝኛ “webpage” ማለት ሲሆን፣ ይህም የአንድ ዌብሳይት አንድ ገጽ ብቻ ነው፡፡ “Website” ማለት በርካታ ገጾች (webpages) እርስ በርስ ተያይዘው (linked ሆነው) የሚገኙበት የገጾች ስብስብ ነው፡፡ ምናልባት አንድ ሰሞን መጥቶ የነበረው “ ድር-አምባ” የሚለው ስያሜ የተሻለ ቅርበት ያለው ቢሆንም፣ ለአብዛኛው ሰው የሚከብድ ስለሚሆን “ዌብሳይት” የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል እንዳለ ብትጠቀሙበት የተሻለ ነው እላለሁ፡፡
ሌሎች ማስተካከያዎችን በቀጣይ አቀርባለሁ፡፡

Sunday, November 18, 2018

እስቲ “ፍትህ ለኢትዮጵያ” እንበል!


... 1871 በፈረንሣዊው ዩጂን ፖቲየ የተደረሰውና የግራ-ዘመሞች (በዋናነት የሶሻሊስቶች) መዝሙር የሆነውንኢንተርናሲዮናልበልጅነታችን በትምህርት ቤት የዘመርን ሁሉ እናስታውሰዋለን፡፡ በግጥሙ ውስጥ ካሉት ስንኞች መካከል፡-
ፍትህ በሚገባ ይበየናል፤
ሻል ያለ ዓለምም ይታያል፡፡
--
የሚሉ ይገኙበታል፡፡
የሶሻሊስታዊያንና የግራ-ዘመሞች የፍትህበሚገባ የመበየንምኞት ሙሉ በሙሉ ዕውን ሳይሆን ቀርቶ፣ በምትኩ ፍትህ-አልባነት መገለጫቸው ሆኖ እስከ ኮሙኒዝም ፍጻሜ ድረስ ቀጥሏል፡፡ አሁንም ቢሆን፣ በግራ ዘመም የፖለቲካ አራማጅ ኃይሎች የሚመሩ በርካታ አገራት ፍትህ-አልባነት ዋነኛ መለያቸው እንደሆነ ቀጥሏል፡፡ 
አገራችን ኢትዮጵያም፣ በተለይ 1966 አብዮት አንስቶፍትህ፣ እኩልነት፣ ነጻነትየሚሉ መፈክሮች ሲስተጋቡባት የኖረች ብትሆንም፣ ቃልና ተግባር ያልተገናኙባት፣ እንዲያውም በተቃራኒው፣ ከቀደሙት ዘመናት በከፋ መንገድ እነዚህ መብቶች የተረገጡባት ምድር ሆናለች። ለመብቶቹ መረጋገጥ በርካታ ዓመታትን የወሰዱና ከፍተኛ መስዋዕትነት ያስከፈሉ ትግሎች ተካሂደውጨቋኝየተባሉ አስተዳደሮች ቢወገዱም፣ በምትካቸው የመጡት አሸናፊዎች ከመሻል ይልቅ እየባሱ፣ ከመምራት ይልቅ እየገዙና የጭካኔ መንገዳቸውንም እያከፉ ለሌላ ዙር አመጽና ትግል በር ሲከፍቱ፣ በዚህም ትግል እነርሱም ከወንበራቸው በመፈንገል አዙሪቱን አስቀጥለውታል፡፡ 
በእያንዳንዱ የአገዛዝና የወንበር ለውጥ ማግሥት፣ የተለያዩ የሕዝብ ጥያቄዎች፣ የተዳፈኑበትን አመድ እያራገፉ ወደ አደባባይ መውጣታቸው የተለመደ ነው፡፡ ዜጎች በተለያዩ አደረጃጀቶችአሉንየሚሏቸውን ጥያቄዎች ይዘውፍትህ ይሰጠንበማለት በተለያዩ መንገዶች ድምጻቸውን ያሰማሉ፡፡ ጥያቄዎቻቸው ምንም ያህል የተለያዩ ቢሆኑም፣ ማጠንጠኛቸው በዋናነትፍትህ አጣንየሚል ነው፡፡
ይህ የፍትህ ጥያቄ እጦት ጉዳይ መሬት የረገጠና በተጨባጭ የሚታይ፣ በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች በተለያየ ደረጃ ሊገለጽ የሚችል ነው፤ ስለሆነም የፍትህ ጥያቄዎች እዚህም አዚያም ጎላ ብለው ቢደመጡ የሚገርም አይደለም። ለጥያቄዎቹም ምላሽ መስጠት በዋናነት ከመንግሥት የሚጠበቅ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡
በዚህ አግባብ ከዛሬ ሦስት ዓመታት በፊት በአገራችን የተለያዩ ክፍሎች የሕዝብ ብሶትን መነሻ አድርገው የተቀጣጠሉ ተቃውሞዎች በመንግሥት አመራር ላይ ከዚህ ቀደም ባልታየ ሁኔታ ለውጥ እንዲፈጠር መንስኤ መሆናቸው የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው፡፡ በዚህ ለውጥ ባለፉት ሰባት ወራትይሆናሉተብለው ያልተጠበቁ መሻሻሎች በፍጥነት እያየን ነው፡፡ ይህ በራሱ መልካም ጅምር ሆኖ ወደፊትም በተጠናከረ ሁኔታ እንዲቀጥል የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ፍላጎት መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ ከዚህ መልካም ጅማሮና ከተገኙ ውጤቶች ጎን ለጎን፣ በርካታ ያልተፈቱና ሕዝቡ አሁንም እንዲፈቱለት የሚጠይቃቸው በርካታ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ኅብረተሰቡም በተለያዩ መንገዶች ጥያቄውን ማቅረቡን አላቋረጠም፡፡
እነዚህን ጥያቄዎች ለማቅረብ በሰላማዊ ሰልፍ፣ በማኅበራዊ ሚዲያዎችና በሌሎችም መንገዶች ከሚስተጋቡ መፈክሮች መካከልፍትህ ለእከሌ፣ፍትህ ለእነ እንቶኔ፣” “ፍትህ ለዚህ ሕዝብ….” የሚለው ዋነኛው ነው፡፡ ጥያቄዎቹ በዚህ መልክ መነሳታቸው ምንም ክፋት ባይኖረውም፣እንደኔ እምነት፣ ሁሉንም የሚጠቀልል አንድ መፈክር ያስፈልገናል - “ፍትህ ለኢትዮጵያ!”
ለምንፍትህ ለኢትዮጵያ!”?
ከፍ ብዬ እንደገለጽኩት፣ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት (በተለይም 1966 አብዮት ማግሥት አንስቶ) ከፍ ያለ የፍትህ እጦት ከዳር እስከ ዳር ያስተናገደች አገር ናት፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውና አሁንም ሙሉ በሙሉ ያልጠፋው የፍትህ እጦት ዘር፣ ብሔር፣ ቋንቋ፣ ሃይማኖት፣ የኑሮ ደረጃ፣ሳይለይ በሁሉም ኢትዮጵያዊያን ላይ የጭካኔ በትሩን ያሳረፈና እያሳረፈ ያለ ክፉ ጠላታችን ነው፡፡ በዚህ ምክንያትም ይመስለኛል፣ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያንእገሌ ከእገሌሳይባል፣ ደረጃው ቢለያይም እንኳ ስለ ፍትህና ርትዕ መጓደልና አለመኖር የምናማርረው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ በሚገባ የተበየነበት አንድም ክልል የለም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ርትዕ ለሁሉም በእኩል መጠን የሆነለት አንድም ማኅበረሰብ የለም፡፡ በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው እንዲሁም በማኅበራዊው ዘርፍ፣የምፈልገውንና የሚገባኝን ሁሉ በሥርዓት አግኝቻለሁየሚል የማኅበረሰብ ክፍል ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ ሁሉምጎደለብኝ፣ ቀረኝ፣ አነሰኝየሚል ቅሬታ አለው፡፡ ይህንን ስናይ፣ ፍትህ የተጓደለው፤ለአንድ ወይም ለተወሰኑ አካባቢዎችና ማኅበረሰቦች ብቻ ሳይሆን፣ ለመላዋ ኢትዮጵያ ነው፤ ብለን እንድናምን ያስገድደናል፡፡ 
የአገር ፍትህ ማጣት የሁላችንም ፍትህ ማጣት ነው፣ የአገር ርዕት-አልባ መሆን የሁላችንም ርዕት-አልባነት ነው፡፡ በአንደኛው ክልል፣ ዞን፣ ወረዳ፣ ቀበሌ፣ ወይም ጎጥ የሚታይ የፍትህ እጦት፣ ይዘገይ እንደሆን እንጂ በሁላችንም ቤት መግባቱ አይቀርም፡፡ ይህን ማስቀረት የሚቻለው አገር በሁሉም መስክ ፍትህ በሚገባ ሲበየንባት ብቻ ነው፡፡
ስላጣነው ፍትህና ርትዕ በያለንበት መጮኻችን አግባብ ነው፣ ነገር ግን የፍትህ እጦቱ በተለይ ባለፉት 27 ዓመታት እንደታዘብነው፣ ተቋማዊና አገር-አቀፋዊ መልክና ቅርጽ ያለው፣ አልፎ ተርፎም የፖለቲካ የበላይነት ማረጋገጫ እስከመሆን የደረሰ፣ በአንዳንድ መልኩም የመጨቆኛ መሣሪያ ለመሆን እንደበቃ ተበዳዩ ሕዝብ ሲናገር ይሰማል፡፡ ይህንን አገር-አቀፍ ችግር ለመዋጋት አገራዊ ፍትህ ወሳኝ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የየራሳችንን የፍትህ ጥያቄ ብቻ አስመልሰንሁሉም ጥሩ ነውብለን አርፈን ለመተኛት አንችልም፡፡ የሌላው ችግር በአንድ ወይም በሌላ መንገድ እኛው   መምጣቱ አይቀርም፡፡ ይህ እንዳይሆን፣ አገራዊ ፍትህ ለኢትዮጵያ ያስፈልጋታል፡፡
ስለዚህ፤ የየቡድናችን፣ የየማኅበራችን፣ የየብሔረሰባችን፣ የየብሔራችን፣ የየክልላችን፣ፍትህ በማያዳግም መልኩ እንዲረጋገጥ፣ እስቲፍትህ ለኢትዮጵያ!” እንበል፡፡ አዎ፤ፍትህ ለኢትዮጵያ”!!