Tuesday, September 9, 2014

ደጋፊ! ደጋፊ! ደጋፊ!

ይህንን ጽሑፍ እየጻፍኩ ያለሁት ብዙ ጊዜ ኳስ ከማይበት የመዝናኛ ሥፍራ ቁጭ ብዬ ነው፡፡ ከፊት ለፊቴ ባለው ቴሌቪዥን ላይ ባለፈው የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ የውድድር ዓመት በሁለቱ የማንቸስተር ከተማ ክለቦች (ማንቸስተር ሲቲ እና ማንቸስተር ዩናይትድ) መካከል በኢትሃድ ስታዲየም (የማንቸስተር ሲቲ ሜዳ) ላይ የተካሄደው ጨዋታ እየተላለፈ ነበር፡፡ የዚህ ጨዋታ ውጤት ለዩናይትዶች አሸማቃቂና አሳፋሪ ነበር፡፡ አራት ለ አንድ!
ይህ ጨዋታ ከተካሄደ ዓመት ሊሆነው ስለተቃረበና ውጤቱንም የማውቀው ስለሆነ ትኩረቴ ጨዋታው ላይ አልነበረም፣ ከዚህ ይልቅ ትኩረቴበስታዲየሙ ተገኝተው ጨዋታውን እየተከታተሉ በነበሩት ተመልካቾች ላይ ነበር፡፡ የማንቸስተር ዩናይትድ ደጋፊዎች ቡድናቸው እንደዛ እየተቀጠቀጠ ባለበት ወቅት አኩርፈው ከመቀመጥ ይልቅ በተቻላቸው አቅም ሁሉ ተጫዋቸቻቸውን ከማበረታታት አልቦዘኑም ነበር፡፡ ብስጭታቸው ፊታቸው ላይ እየተነበበ ቢሆንም፣ እዚያ ቦታ የተገኙበትን ምክንያትና ዓላማ አልዘነጉምና ማድረግ ያለባቸውን አድርገው ጨዋታውን እንደምንም ጨረሱት፡፡
ይህንን ለተመለከትሁ በኋላ፣ እኛስ እንዴት ነው የምንደግፈውን ቡድን የምናበረታታው? የሚለውን ጥያቄ ማሰላሰል ጀመርኩ፡፡ ለዚህ ሐሳቤ ደግሞ ተጨማሪ መነሻ ነበረኝ፡፡ ባለፈው ቅዳሜ ለ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የመጀመሪያው ዙር የመጀመሪያ የማጣሪያ ጨዋታዎች ሲካሄዱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም ከአልጄሪያ አቻው ጋር ተጋጥሞ ነበር፣ በውጤቱም 2-1 ተሸንፏል፡፡ ታዲያ በዚህ ጨዋታ ላይ እንደቀደሙት ጊዜያት ሁሉ በስታዲየሙ የታደሙ የዋሊያዎቹ ደጋፊዎች ተመልካች ብቻ ሆነው መገኘታቸው ቅር አሰኝቶኝ ስለነበረም ጭምር ነው ይህ ጥያቄ የተፈጠረብኝ፡፡
"ደጋፊነት" ምን ማለት ነው? እኔ እንደሚገባኝ አንድ ሰው የአንድ ግለሰብ፣ ተቋም ወይም ስብስብ ደጋፊ ሲሆን፣ ለሚደግፈው አካል ዓላማና ተግባር መሳካት በበኩሉ ማድረግ የሚገባውን ነገር (ማበረታታት፣ በገንዘብ ወይም በጉልበት ወይም በሐሳብ እገዛ ማድረግ፣ በተደጋፊው አካል በሚደረግለት ጥሪ መሠረት መሳተፍ፣ ወዘተ) ማድረግ ነው፡፡ በዚህ የደጋፊነት ሚና ውስጥ ታዲያ፣ ተደጋፊው አካል በጉዞው ላይ አስፓልትም ሆነ ኮረኮንች መንገድ ቢያጋጥመው፣ ሜዳማ ወይም ተራራማ ቦታ ላይ ቢደርስ፣ የተራራው አናት ላይ ቢወጣ ወይም በሸለቆው ውስጥ ቢገባ፣ ዓላማውን እስካመነበት ድረስ ደጋፊው “አይዞህ! አለሁልህ! በርታ!” ሊለው ግድ ይላል፡፡ ይህንን ማድረግ ተስኖት፣ ሲወድቅ  “ይድፋህ!” የሚለው ከሆነ፣ አንድም ደጋፊ አይደለም፣ አንድም ደጋፊነትን አያውቀውም፡፡
ከዚህ ተነስተን የቅዳሜውን የአዲስ አበባ ስታዲየም ድባብ ስንመለከት፣ በአብዛኛው ኢትዮጵያውያኑ ታዳሚዎች “ደጋፊዎች” ሳይሆኑ “ተመልካቾች” ነበሩ ማለት ያስደፍራል፡፡ ይህ ክስተት ደግሞ አዲስ ሳይሆን፣ ለዓመታት ስናየው የኖረ ነው፡፡ ዛሬ ግን በደንብ ልናስብበት የሚያስፈልገውድጋፍ ከጭብጨባና ፉጨት ባለፈ ትልቅ ጉልበት ያለው መሣሪያ መሆኑን መረዳት ስለሚያስፈልግ ነው፡፡ በተለይ በእግር ኳሳችን ላይ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ እየታየ ካለው አንጻራዊ መሻሻል አንጻር በሜዳላይ ለሚጫወቱ ተጫዋቾች የምንሰጠው ድጋፍ ለዕድገቱ መቀጠል አስፈላጊ መሆኑን ማወቅ አለብን፡፡ ደጋፊ ሆነን የምናሰማው ዝማሬ፣ ጭብጨባ፣ ፉጨት፣ ወይም ጩኸት ለተጫዋቾቻችን የሞራል ስንቅና የሥነ-ልቦና ጉልበት መሆኑን ልብ ልንል ይገባል፡፡ የሚመቱት ኳስ ዒላማውን ባያገኝ ወይም የተጋጣሚ ቡድን ጎል ቢያገባ እንደተቆጡት ሕጻን እጅን ከንፈር ላይ አድርጎ መቀመጥ ለምንደግፈው ብድን እንደማይጠቅም ካላወቅንና የጨዋታውን እንቅስቃሴ ብቻ በመከታተል ጊዜውን የምናሳልፍ ከሆነ ገንዘብ ከፍለን ስታዲየም ከምንገባ በየቤታችን ቁጭ ብለን በነጻ በቴሌቪዥን ብንመለከት ይሻላል፡፡ ኧረ እንዲያውም ሰው ሰብሰብ ባለበት ቦታ ከሆነ ድጋፉም ከስታዲየሙም ይበልጣል! እኔ ጨዋታውን በተመለከትኩበት ቦታ (ይህ ጽሑፍ የተጻፈበት ቦታ ነው) ዝማሬውና ሆታው ሁለተኛው የአልጄሪያ ጎል ከተቆጠረ በኋላም አልተቋረጠም ነበር፡፡

ስለዚህ ጎበዝ! ደጋፊ እንጂ ተመልካች አንሁን፡፡ መመልከት ለመዝናናት መጥቀሙ ባይካድም፣ ስታዲየም ስንገባ የምንደግፈውን ቡድን ለማበረታታት መሆኑንም መዘንጋት የለብንም፡፡ ተጫዋቾቻችን የእኛን ድጋፍ በእጅጉ ይፈልጋሉና ዝም አንበላቸው፡፡ በአውሮፓው እግር ኳስ እኮ የጨዋታው ውበት የሜዳው ላይ እንቅስቃሴ ብቻ ሳይሆን የደጋፊዎቹ የማያቋርጥ ዝማሬና ጩኸትም እንደሆነ በቴሌቪዥንም እናያለንና፣ ከኮረጅን አይቀር እንደቴክኒኩ ሁሉ አደጋገፉንም አብረን ብንኮርጅ ምን ይለናል?

Friday, May 30, 2014

ካርል፣ ከኢትዮጵያዊ በላይ ኢትዮጵያዊ!


እነሆ! ትናንት ባለውለታችንን አጣን፡፡ የቁርጥ ቀን የኢትዮጵያ አጋር፣ ከራሱ ዝናና ክብር በላይ ለሌሎች የመኖር ጉጉት አይሎበት፣ ምቾትና ድሎቱን ለሰብአዊነት ሲል ትቶ፣ችግራችንን ተቸግሮና በደስታችን ተደስቶ 33 ዓመታትን ከኢትዮጵያዊያን በላይ ኢትዮጵያዊ ሆኖ የኖረው ካርልሃይንዝ ቦም በ86ኛው ዕድሜው ላይ ለሞት እጁን ሰጠ፡፡ ሰው ሆኖ ኖሮ የማይሞት አለመኖሩ የማይቀር ቢሆንም፣ እንደካርል ዓይነቱ ልበ-ብርሃን ግን ሲሞት ብዙ ያጎድላል፡፡
ይህ ካርልሃይንዝ ቦም የሚባል ሰው የበርካታ ገድሎች ባለቤት ነው፣ ታሪኩ ትልቅ መጽሐፍ የሚወጣው፡፡ ከእኔ በላይ ብዙ ሊናገሩ የሚችሉ ሰዎች አሉና ብዙ ልል አልችልም፡፡ ሰውየውን ለማስታወስ ግን ከእርሱ ጋር የሚያያዙና በጣም የሚነኩኝን ሦስት  ነገሮች ብቻ ላንሳ፡፡
1.      ካርል ለበጎ አድራጎት ሥራው ወደ ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የመጣው በ1973 ዓ.ም. ነበር፡፡ ነገር ግን በቀጥታ አልነበረም ወደዚህ የመጣው፡፡ ወቅቱ በርካታ የአፍሪካ አገሮች የድርቅ አደጋ ያንዣበበባቸው ወቅት ነበርና፣ ካርልም የድርቁ አደጋ የከፋባቸውን የሳህል አገሮችን ለመርዳት አስቦ ነበር ወደአፍሪካ የመጣው፡፡ በመጀመሪያ ቻድ ሄደ፣ የቻድ መንግሥት አልተቀበለውም፡፡ ቀጥሎ ወደሱዳን አቀና፣ የካርቱምም ምላሽ ተመሳሳይ ነበር፡፡ በሦስተኛ ሙከራው ወደ አዲስ አበባ ሲመጣ ግን የወቅቱ መንግሥት በደስታ ነበር የተቀበለው፤ ያለቢሮክራሲያዊ ውጣ-ውረድ፣ ”እስቲ የመደብ ጀርባው ይጠና ” ሳይባል፡፡ ይህ ለኢትዮጵያ ያሳየው ተቆርቋሪነትና የተደረገለት አቀባበል ግን በሁሉም ወገን በኩል በቀና አልታየም፡፡ በተለይ በጊዜው በስደት በምዕራብ አገሮች የነበሩ ኢትዮጵያዊያን ”ይህ የምዕራብ አገር ሰው ከደርግ ጋር መሥራቱ ክህደት ነው” በሚል ከፍተኛ የተቃውሞና አለፍ ሲልም የስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍተውበት ነበር፡፡ ነገር ግን ካርል፣ ”ሰብአዊ አገልግሎትና ፖለቲካ ለየቅል ናቸው፡፡ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ይልቅ ሰብአዊነት ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል” በሚል ጽኑ አቋም፣ የተከፈተበትን ዘመቻ ከቁብም ሳይቆጥር ሥራውን ቀጠለ፡፡  ኢትዮጵያም ደርሶ ከ33 ዓመታት በፊት ”ሰዎች ለሰዎች” (Menschen für Menschen) የተባለውን ምግባረ-ሰናይ ድርጅቱን በመመሥረት በጤና እክል ምክንያት ሥራውን እስካቆመበት እስከ 2003 ዓ.ም. ድረስ በሊቀመንበርነት መርቶታል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ግን እንደ ድርጅቱ ሠራተኛ አንድም ጊዜ ደመወዝ ሳይወስድ በነጻ ነበር ታላላቅ ሥራዎችን የሠራው፡፡
2.     ”ሰዎች ለሰዎች” ሥራውን በጀመረበት የኤረር ሸለቆ አካባቢ የፕሮጀክቱ ተጠቃሚ ከነበሩት ሰዎች መካከል አብዲ አሊ ቦሩ አንዱ ነው፡፡ አብዲ፣ እንደሌሎቹ ተጠቃሚዎች ሁሉ ለካርል ከፍ ያለ ፍቅር ቢኖረውም፣ የፍቅሩ መግለጫ ግን የተለየ ነበር፡፡ ማንም ሳያዘው፣ ሳይቀጥረውና ደመወዝ ሳይከፍለው፣ ካርል ወደ ቦታው በመጣ ጊዜ ሁሉ፣ እዚያ በሚገኘው ቤቱ በር ላይ ማታ ማታ እየተኛ፣ ክፉ እንዳያገኘው ሲጠብቀው ያድራል፡፡ ካርል ጠዋት ተነስቶ በሩን ሲከፍት መጀመሪያ የሚያየው ደጃፉ ላይ ጥቅልል ብሎ የተኛውን አብዲን ነበር፡፡ ታዲያ አብዲ ይህንን ለምን እንደሚያደርግ ሲጠየቅ፣ ”ካርል ለእኔ አባቴ ነው፡፡ አባቴ ያላደረገልኝን ነገር አድርጎልኛል፡፡ ታዲያ ይህ ሰው አንድ ነገር ቢሆን ምን ይውጠኛል? መጥፎ ነገር ቢመጣ እንኳ መጀመሪያ እኔን ያግኘኝ ብዬ  ነው፡፡” ብሎ ነበር፡፡ ካርልም ለአብዲ ያለው ፍቅር እጅግ የበዛ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ለድርጅቱ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ጀርመን ላይ ተካሂዶ ነበር፡፡ በዚህ ሰፊ የቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ሽፋን ባገኘ ፕሮግራም ላይ  ታዲያ አዘጋጆቹ ካርልን ሰርፕራይዝ ያደረጉት በአብዲ ነበር፡፡ አብዲ ሽርጡን እንዳሸረጠ ወደመድረኩ ሲመጣ ካርል ዓይኑን አላመነም ነበር፡፡ ትልቁን ሰውዬ እንደ ሕጻን ልጅ አገላብጦ ነበር የሳመው፡፡ ”ታማኝ ወዳጄ” ሲልም አሞግሶታል፡፡ ካርል ለሠራቸው በጎ ሥራዎቹ ሁሉ ተጠቃሚዎቹ አመስግነውት አይጠግቡም፡፡ በ1995 ዓ.ም. ”ሰዎች ለሰዎች” በሰሜን ሸዋ መሐል ሜዳ ላይ ያሠራው ”ካርል ሆስፒታል” በተመረቀበት ወቅት አንድ የአካባቢው አርሶ አደር ሲናገሩ (ቃል በቃል ላይሆን ይችላል) ”በፊት ሕክምና በዚህ ባልነበረ ጊዜ በትንሽ ሕመም እንኳ ብዙ ሰው ይሞትብን ነበረ፡፡ ቃሬዛ ሠርተን ተሸክመን ወደ ከተማ እየወሰድን መከራችንን ስንበላ ኖርን፡፡ አሁን ግን ካርል ከመጣ በኋላ ሰዉ ሆዴን ቆረጠኝ፣ ራሴን ፈለጠኝ ቢል ከዚሁ ከጓሯችን ሂዶ ክኒናውን እየዋጠ ጤና ሆነ፣ እኛም ይኸው ካርልን ያኑርልን እያልን ደስ ብሎን አለን፡፡” ብለው ነበር፡፡ ከዚህም በላይ ብዙ ምስጋናና ምርቃትም አግኝቷል፡፡
3.     ከዛሬ 8 ዓመት በፊት የ”ሰዎች ለሰዎች” 25ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን ምክንያት በማድረግ በጀርመን የባሕል ተቋም (ጎተ ኢንስትቲዩት) በተዘጋጀ ፕሮግራም ላይ ተገኝቼ ነበር፡፡ በረጅም ጊዜ የተቋሙ ደንበኝነቴ አዳራሹ እንደዚያ ቀን ሞልቶ ያየሁበትን ቀን አላስታውስም ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ካርል ነበር፡፡ በዚያው ሰሞን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይቀርብ በነበረው ”ዐውደ-ሰብ” የተባለ ፕሮግራም ካርልን የተመለከተ ሰፊ ዝግጅት ቀርቦ ስለነበር ብዙ ሰዎች ለካርልና ለ”ሰዎች ለሰዎች” ግምታቸው ከፍ ብሎ ስለነበር ይመስለኛል፡፡ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን ነበረ፣ ከካርል ጋር አብረው የሠሩና ካርልን የሚያውቁ ታዋቂ ሰዎች ምስክርነታቸውን ሰጡ፣ በመጨረሻ ላይ ካርል ንግግር አደረገ፡፡ ከንግግሩ መካከል እስከዛሬ የማይረሳኝ ”ዛሬ ኢትዮጵያ አገሬ ሆናለች፡፡ አገሬን ደግሞ ተለውጣ ላያት እመኛለሁ፡፡ አሁን የናፈቀኝ እናንተ ‘ዛሬ ራሳችንን ችለናልና ላደረጋችሁልን ሁሉ እናመሰግናለን፡፡ ካሁን በኋላ ግን አንፈልጋችሁም ‘ የምትሉበትን ቀን ነው፡፡” ያለውን ነው፡፡ ይህንን ሕልሙን ዕውን ሆኖ ሳያየው ሞት ቀደመው፡፡

ዛሬ ካርል አርፏል፡፡ የእርሱ ዕረፍት ደግሞ ራሳችንን እንድንጠይቅ ያደርገናል፡፡ ”እኛ ኢትዮጵያዊያን ለኢትዮጵያ ምን አደረግን?” የሚል ጥያቄ፡፡ ይህ ሰው፣ ምኑም ያልሆነች አገር ችግር ቢያመው፣ ብዙ ሐብት ያፈራበት የነበረውን የቴአትርና የፊልም ተዋናይነቱን ትቶ፣ ያለውን ሁሉ ለዚህች አገር ሲሰጥ፣ እኛ ያገር ተወላጆቹ ”ምን ሠራን?” ብንል መልሱ ያሳፍረናል፡፡ በተለይ፣ ”ባለሐብት” የሚባሉት (ከጥቂቶች በስተቀር)፣ ያላቸውን በሙሉ ባይሰጡ እንኳን፣ ከዓመታዊ ትርፋቸው ላይ ጥቂቱን አንስተው በተደራጀ መልኩ ለበጎ አድራጎት ሥራ ሲያውሉ የማይታዩ መሆናቸው አንገት የሚያስደፋ ነው፡፡ ይህ ነው ”ማነው ኢትዮጵያዊ?” የሚያስብለው፡፡ ካርል! ከኢትዮጵያዊ በላይ ኢትዮጵያዊ ሆነህ ኖረህ፣ ኢትዮጵያዊ ሆነህ አርፈሃል፡፡ ውለታህን ግን አንዘነጋውም፡፡ ስናመሰግንህ እንኖራለን፡፡  ምስጋናችን በሁለት ምክንያት ነው፣ አንድም፣ በችግራችን ወቅት ስለደረስክልን፣ ሁለትም፣ራሳችንን እንድንወቅስ  ስላደረከን፡፡